Abiy Ahmed along with Military officials -FILE

ዋዜማ – ጠቅላይ ሚንስትር ዐብይ አህመድ በኢትዮጵያ የውስጥ ጉዳይ እየገቡ “መፈትፈት የሚፈልጉ” “ኢትዮጵያዊ ያልሆኑ ኀይሎች” ከድርጊታቸው እንዲቆጠቡና በራሳቸው ሀገር ጉዳይ ላይ እንዲያተኩሩ አስጠነቀቁ።

ጠቅላይ ሚንስትር ዐብይ ሰኞ ሚያዚያ23 ቀን 2015 ዓ.ም የሀላላ ኬላ መዝናኛ ማዕከልን መርቀው ሲከፍቱ ባደረጉት ንግ ግር መንግስትን ከስልጣን ለመገልበጥ በሚደረግ አመፆ ላይ የሚሳተፉ ባለሀብቶች፣ ወጣቶች እንዲሁም በውጪ ሀገር የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንን ከድርጊታቸው እንዲታቀቡ በብርቱ አሳስበዋል። መንግስት እንደዚህ ቀደሙ “የህግ ማስከበር እርምጃ” ከመውሰድ ወደ ኋላ እንደማይልም ተናግረዋል።

ጠቅላይ ሚንስትሩ በስም ያልጠቀሷቸውን የውጪ ኀይሎችም አስጠንቅቀዋል።

“ኮሽ ባለ ቁጥ በር በኣኢትዮጵያ ውስጣዊ ጉዳይ እየገቡ መፈትፈት የሚፈልጉ ኀይሎች፣ በተለይም ኢትዮጵያዊ ያልሆኑ ኀይሎች ከድርጊታቸው እንዲሰበሰቡ እንዲቆጠቡ ለማሳሰብ እወዳለሁ። ኢትዮጵያን በማበጣበጥ በማባላት የሚገኝ ትርፍ እንደሌለ አውቀው፣ የኛን ጉዳይ ለኛ ትተው፣ በርከት ያለ ያልሰሩት ጉዳይ ስላላቸው፣ ስራዎቻቸውን በምድራቸው ላይ መስራት እንዲችሉ፣ የኛን ጉዳይ ለኛ መተው እንዲችሉ ማሳሰብ እፈልጋለሁ….” ብለዋል ዐቢይ።

ጠቅላይ ሚንስትሩ በኣኢትዮጵያ ጉዳይ መፈትፈት የሚፈልጉ ስላሏቸው ኀይሎች ተጨማሪ ማብራሪያ አልሰጡም።


ባለፉት ሳምንታት የአማራ ክልል ልዩ ኀይልን አፍርሶ ወደ መደበኛ አደረጃጀት ለማስገባት እንቅስቃሴ ከተጀመረ በኋላ በክልሉ የበረታ አለመረጋጋት መከሰቱና ሰፊ ህዝባዊ ተቃውሞ መከሰቱ ይታወቃል።


ባለፈው ሳምንትም የአማራ ክልል ብልፅግና ፅሕፈት ቤት ኀላፊ አቶ ግርማ የሺጥላ በትውልድ አካባቢያቸው ማንነታቸው ባልታወቁ ሰዎች በደፈጣ ጥቃት መገደላቸው ይታወሳል።

የፌደራሉ የፀጥታ አካላት በተለያዩ አማራ ክልል አካባቢዎች አዲስ እርምጃ መውሰድ መጀመራቸውን ከአራት ቀናት በፊት አስታወቀዋል።
በአማራ ክልል ደቡብ ወሎ፣ ሰሜን ሸዋ፣ ደቡብ ጎንደር እና ሰሜን ጎንደር የሚገኙ ምንጮች እንደነገሩን በአካባቢያቸው በርካታ ሰዎች የፋኖ አባላት ናችሁ ተብለው ታስረዋል። ሰሜን ሸዋና ደቡብ ጎንደር አካባቢ ላለፉት ሁለት ቀናት ተኩስ የተቀላቀለበት ግጭት በአካባቢው መኖሩንም ሰምተናል። [ዋዜማ]