logo SDዋዜማ ራዲዮ- የዩናይትድ ስቴት ስ መንግስት ከፍተኛ የልዑካን ቡድን ወደ አዲስ አበባ ይጓዛል።
የአሜሪካ የውጪጉዳይ መስሪያ ቤት ምንጮች ለዋዜማ እንደተናገሩት የልዑካን ቡድኑ በአዲስ አበባ ቆይታው ከኢትዮጵያ መንግስት ባለስልጣናት ጋር ተገናኝቶ ይነጋገራል።

ውይይቱ በኢትዮጵያ የፖለቲካ ማሻሻያና በክፍለ አህጉራዊ የፀጥታ ጉዳይ ላይ ያተኩራል።
ከልዑካን ቡድኑ ጉብኝት አስቀድሞ በአዲስ አበባ የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ በኢትዮጵያ እውነተኛ የፖለቲካ ማሻሻያዎች እንዲደረጉ ለማበረታታት ከተቃዋሚ መሪዎች ከሲቪክ ማህበራትና ከታዋቂ ስዎች ጋር የሀሳብ ማስባሰብ እያደረገ መሆኑን ለጉዳዩ ቅርብ የሆኑ ምንጮች ይገልፃሉ።
መንግስት የፖለቲካ እስረኞችን ለመፍታት ያሳየውን ፈቃደኝነት እንደ በጎ እርምጃ የወሰደው የአሜሪካ መንግስት ተጨማሪ እርምጃዎች እንዲወሰዱ ፍላጎት እንዳለው መግለፁ ይታወሳል።
የአሜሪካ የውጪ ጉዳይ መስሪያቤትና ሁለት ለአሜሪካ መንግስት ቅርብ የሆኑ የጥናት ተቋማት ባለፉት ሳምንታት በውጪ ሀገር ያሉ የተለያዩ ግለሰቦችን ሲያነጋግሩ እንደነበርና ከሀገር ውጪ ያሉ የፖለቲካ ሀይሎች ገንቢ ሚና መጫወት የሚችሉበትን መንገድ ሲያጠያይቁ መስማታቸውን በውይይቱ ተሳትፎ ያደረጉ ዲፕሎማት ነግረውናል።

ከሁለት ወራት በፊት የአሜሪካ የውጪ ጉዳይ መስሪያ ቤት የአፍሪቃ ጉዳይ ረዳት ሀላፊ ዶናልድ ያማማቶ አዲስ አበባን ጎብኝተው ከኢትዮጵያ ባለስልጣናት ጋር ስፊ ውይይት ማድረጋቸው ይታወሳል።

አሁን ወደ አዲስ አበባ የሚጓዘው ቡድንም በዶናልድ ያማማቶ የሚመራ እንደሚሆን ይጠበቃል።

[ተጨማሪ የድምፅ ዘገባ ከግርጌ ያድምጡ]

https://youtu.be/J9DxgSjOAoo