ዋዜማ- ከሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን አባል ኮሚሽነሮች መካከል አንዷ ኃላፊነታቸውን በገዛ ፍቃዳቸው መልቀቃቸውን ዋዜማ ከምንጮቿ ሰምታለች።

ኃላፊነታቸውን በገዛ ፍቃዳቸው የለቀቁት አባል ኮሚሽነር ፤ኮሚሽኑ ከተሾሙለት 11 ኮሚሽነሮች መካከል አንዷ የሆኑት ብሌን ገብረመድኅን ናቸው። 

ብሌን ኃላፊነታቸውን የለቀቁት ‹‹በግል ጉዳይ ምክንያት›› በሚል ባቀረቡት የስራ መልቀቂያ ጥያቄ መሠረት መሆኑን የገለጹት የዋዜማ ምንጮች፤ በኮሚሽኑ በተሰጣቸው ኃላፊነት ምክንያት ‹‹ረጅም ጊዜ ወስዶብኛል›› ያሉትን የዶክትሬት ዲግሪ ትምህርት ለማጠናቀቅ ጊዜ እንደሚያስፈልጋቸው መጥቀሳቸውን ጠቁመዋል።

ኮሚሽኑ የሀገራዊ ምክክር ጉባኤ የሚጀመርበትን ቀን እና አጀንዳዎችን በሀገር ውስጥ መገናኛ ብዙኃን በቀጥታ ሥርጭት ይፋ ባደረገባቸው መርሃ-ግብሮች ላይ ብሌን ያልተገኙ ሲሆን፤ ሌሎች ኮሚሽነሮች ግን በእነዚሁ መርሃ-ግብሮች ላይ ታይተዋል።

ከ 4 አመታት በላይ ከ11ዱ ኮሚሽነሮች መካከል አንዷ በመሆን ያገለገሉት ብሌን፤ ኮሚሽኑ የሀገራዊ ምክክር ጉባኤውን መቃረብ ተከትሎ ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት ጋር ባካሄዳቸው ውይይቶች እና ሌሎች ቅድመ-ዝግጅቶች ላይም አልተሳተፉም።

ዋዜማ፤ ብሌን ከኃላፊነት የለቀቁበትን ምክንያት ከራሳቸውን አንደበት ለመስማት ያደረገችው ተደጋጋሚ ጥረት አልተሳካም። 

ለዋናው የምክክር ሂደት ያልደረሱት ኮሚሽነሮች

ከአንድ ዓመት ገደማ በፊት ኮሚሽነር ተገኘወርቅ ጌጡ (ዶ/ር) በፍቃዳቸው ከኃላፊነት መልቀቃቸውን ዋዜማ መዘገቧ ይታወሳል። ተገኝወርቅ ኃላፊነታቸውን የለቀቁት፣ የምክክር ኮሚሽኑ በመቋቋሚያ አዋጁ የተሰጠውን የሦስት ዓመታት ጊዜ አጠናቅቆ፤ የስራ ጊዜው ለተጨማሪ አንድ ዓመት በተራዘመበት ዋዜማ ነበር።

ተገኘወርቅ በወቅቱ ራሳቸውን ከኃላፊነት ያገለሉት፤ ለኮሚሽኑ ቀደም ሲል በተሠጠው የሥራ ጊዜ ማገልገላቸው በቂ መኾኑን በመግለጽ ነበር።

ሌላኛው አባል ኮሚሽነር ዘገየ አስፋው ደግሞ ከሁለት ወራት በፊት ከዚህ ዓለም በሞት መለየታቸው ይታወሳል።

የኮሚሽነር ተገኘወርቅ ጌቱን ከኃላፊነት መልቀቅ በይፋ ያላሳወቀው ኮሚሽኑ፤ የኮሚሽነር ብሌን ገብረመድኅን ከኃላፊነት መልቀቅን አስመልክቶም፤ ዋዜማ ይህን ዘገባ እስከ አጠናቀረችበት ጊዜ ድረስ ያለው ነገር የለም፡፡ 

ኮሚሽኑ ከ 1 አመት በፊት ከሃላፊነታቸው በለቀቁት ተገኘወርቅም (ዶ/ር) ይሁን፤ በቅርቡ በሞት በተለዩት ኮሚሽነር ዘገየ አስፋው ምትክ፤ ሌላ ኮሚሽነር እንዲሾምለት ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ያቀረበው ጥያቄ እንደሌለም ምንጮች ጠቁመዋል።

የኮሚሽነር ብሌን ከኃላፊነት መልቀቅን ተከትሎም በቦታቸው ተተኪ ኮሚሽነር እንዲሾም ጥያቄ ይቀርባል ተብሎ እንደማይጠበቅ በመጥቀስ፤ ኮሚሽኑ በቀጣዮቹ ወራት በቀሪዎቹ 8 ኮሚሽነሮች እንደሚመራም ምንጮች ነግረውናል። 

አዋጁ ምን ይላል?

የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ማቋቋሚያ አዋጅ ኮሚሽነሮች በገዛ ፈቃዳቸው ከኃላፊነት መልቀቅ እንደሚችሉ ደንግጓል። በአዋጁ ላይ ፤ ‹‹ማንኛውም ኃላፊነቱን በገዛ ፍቃዱ መልቀቅ የሚፈልግ ወይም የለቀቀ ኮሚሽነር፤ የሁለት ወር የጽሑፍ ቅድመ ማስጠንቀቂያ ለኮሚሽነሮች ምክር ቤት እና ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ-ጉባዔ በማስገባት ሊለቅ ይችላል›› በሚል ሠፍሯል።

በዚሁ አዋጅ መሠረት፣ አንድ ኮሚሽነር ከኃላፊነት ሲነሳ፣ ሲለቅ ወይም በሞት ምክንያት ሲለይ አዲስ ተሿሚ ይተካል። የተተኪ ኮሚሽነር ሹመትም የሚሰጠው በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሲሆን፤ ተተኪው ከዚህ ቀደም ተጠቁመው በኮሚሽነርነት ካልተሾሙ ዕጩዎች መካከል ተመርጦ እንደሚሾም ተደንግጓል። አንድ ኮሚሽነር ኃላፊነቱን በገዛ ፍቃዱ ከለቀቀ ወይም ከኃላፊነቱ ከተነሳ በኋላ፤ ወዲያውኑ ወደ ሌላ የመንግሥት ሃላፊነት መሸጋገር አይችልም። ‹‹ለሁለት ዓመታት ለሌላ መንግሥታዊ ኃላፊነት ወይም ለፖለቲካ ፓርቲ ሥራ አይታጭም ወይም አይሾምም›› በሚል ተደንግጓል፡፡

የሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን ማቋቋሚያ አዋጅ ቁጥር 1265/2014 ጥር 5 ቀን፤ 2014 ዓ.ም በነጋሪት ጋዜጣ ታትሞ ከወጣ በኋላ፤ በዚያው ዓመት የካቲት 14 ቀን፤ 2014 ዓ.ም 11 ኮሚሽነሮች ተሹመዋል። ኮሚሽኑ ኮሚሽነሮች ከተሾሙለት ዕለት አንስቶ የሚታሰብ የሦስት ዓመታት የሥራ ግዜ እንደሚኖረው የደነገገ ቢሆንም፤ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ኮሚሽኑ ‹‹ሥራውን በተቀመጠለት ጊዜ ውስጥ ማጠናቀቅ አልቻለም›› በሚል ለሁለት ጊዜያት ያህል የሥራ ጊዜውን አራዝሞለታል። ከዚህ ቀደም ከተራዘመው የአንድ ዓመት የሥራ ጊዜ በኋላ የተጨመረው የስምንት ወራት የሥራ ጊዜም ጥቅምት 14 ቀን፤ 2019 ዓ.ም ይጠናቀቃል።

ኮሚሽኑም በተጨመረለት የሥራ ጊዜ መሠረት ሀገራዊ ምክክር ለማካሄድ፤ ከሐምሌ 8 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ ‹‹ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ›› ለማካሄድ 4 ሺሕ የሚደርሱ ‹‹ተመካካሪዎች›› አዲስ አበባ መግባታቸውን ገልጿል።[ዋዜማ]