ዋዜማ ራዲዮ- የሙስና  ተጠርጣሪዎች ቁጥር በየዕለቱ እያሻቀበ ባለበት በአሁኑ ወቅት ለእረፍት የተበተኑ የፓርላማ አባላት በሚቀጥለው ሳምንት መጀመርያ ወደ መዲናው ገብተው ሪፖርት እንዲያደርጉ በምክትል አፈጉባኤዋ መታዘዛቸው ታውቋል፡፡
ፓርላማው በዚህ ጥድፊያ ለምን እንደተጠራ ባይታወቅም ምናልባት ከሰሞኑ ያለመከሰስ መብቱ የሚነሳ ባለሥልጣን ይኖር ይሆን የሚለውን ግምት አጠናክሮታል፡፡ በሰኔ መጨረሻ የተበተነው ፓርላማ ለመጨረሻ ጊዜ የተመለከተው ጉዳይ ሰኔ 22 ኦሮሚያ ክልል ከአዲስ አበባ ይገባኛል የሚለውን ልዩ ጥቅም በተመለከተ ሲሆን ‹‹በቂ የመወያያ ጊዜ ያስፈልጋል›› በሚል ጉዳዩን ወደ 2010 ማዛወሩ ይታወሳል፡፡
ፓርላማው በመጪው ዓመት የመጀመርያ ወር የመጨረሻ ሳምንት ሥራውን እንደሚጀምር ቢታወቅም አሁን በፍጥነት እንዲሰበሰብ ጥሪ መደረጉ በርካታ መላምቶች እንዲፈጠሩ ምክንያት ሆኗል፡፡ በተለምዶ አብዛኛዎቹ የፓርላማ አባላት በእረፍት ጊዜያቸው ወደመረጣቸው ሕዝብ ተመልሰው ይሄዳሉ ቢባልም ይህ ተግባር በኢህአዴግ አባላትና አጋር ድርጅቶች በተሞላው ሸንጎ እምብዛምም የተለመደ አይደለም፡፡ ይልቁንም ክረምቱን አብዛኛዎቹ የምክር ቤቱ አባላት በገርጂና በፒኮክ በሚገኙ አፓርትመንቶቻቸው ሻይ ቡና እያሉ የሚያሳልፉት ቁጥር ከፍተኛ ነው፡፡
በምን ጉዳይ ለመምከር ምክር ቤቱ በዚህ ጥድፊያ ጥሪ ሊያስተላልፍ ይችላል በሚል በዋዜማ የተጠየቁ አንድ የቀድሞ የምክር ቤት አባል ምናልባት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን በተመለከተ ሊሆን እንደሚችል ግምታቸውን ሰጥተዋል፡፡ በ4 ወራት የተራዘመው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የሚያበቃው እንደ አውሮፓዊያን አቆጣጠር በኦገስት 9፣ 2017 መሆኑ ይታወቃል፡፡