Gemshu-Beyene

ዋዜማ ራዲዮ- በኢህአዴግ ታሪክ ሦስተኛው እንደሆነ የተነገረለት የጸረ ሙስና ዘመቻ ካለፈው ሳምንት ጀምሮ አይነኬ የሚመስሉ ባለሐብቶችንና ድርጅቶችን በር ማንኳኳት የጀመረ ይመስላል፡፡ በአገሪቱ ግዙፍና ስመጥር የመንገድና የሕንጻ ተቋራጮች ሒሳባቸው እንዳይንቀሳቀስ በፍርድ ቤት እግድ መጣሉ ለዚህ እንደማስረጃ እየተጠቀሰ ነው፡፡
ከነዚህ ግዙፍ ተቋራጮች መካከል ስመጥሮቹ አሰር ኮንስትራክሽንና ገምሹ በየነ (Gemecon) ደረጃ አንድ ጠቅላላ ኮንትራክተር ይገኙበታል፡፡ የገመኮን መንገድ ተቋራጭ ድርጅቱ ባለቤት አቶ ገምሹ በየነ ከጥቂት ቀናት ጀምሮ የት እንደገቡ አልታወቀም ተብሏል፡፡ የዋዜማ ሁነኛ ምንጮች እኚህ ስመጥር ባለሀብት ከአገር ሾልከው ሳይወጡ እንዳልቀረ ይጠረጥራሉ፡፡ ምክንያታቸውን ሲያስረዱም ባለፉት ሰባት ቀናት ውስጥ ቢሯቸው አለመግባታቸውን ያነሳሉ፡፡
አንድ የኢሊሌ ሆቴል የጥበቃ ባልደረባ ከሁለት ሳምንት በፊት ጸጉራቸውን በራሳቸው ሆቴል ውስጥ በሚገኝ የውበት ሳሎን ሲስተካከሉ እንደተመለከቷቸውና ከዚያ ወዲህ ግን ወደ ሆቴላቸው ዝር እንዳላሉ ማረጋገጫ ሰጥተዋል፡፡ በስም መጠቀስ ያልፈለገ ሌላ የሆቴሉ ማኔጅመንት አባል ‹‹ለዕቃ ግዢ ከአገር መውጣታቸውን ነው የማውቀው፤ በእርግጠኝነት ይመለሳሉ›› ሲል ተናግሯል፡፤
በአገሪቱ ከሚገኙ በጣት ከሚቆጠሩ ባለ አምስት ኮከብ ሆቴሎች አንዱ የሆነውና በካዛንቺስ አካባቢ የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን (ኢሲኤ) ጀርባ የሚገኘው ኢሌሌ ኢንተርናሽናል ሆቴል በአቶ ገምሹ በየነ ባለቤትነት የተያዘ ግዙፍ ሆቴል ሲሆን ከአዲስ አበባ መስተዳደር በቅርብ አመታት ውስጥ ባገኘው 1690 ካሬ የማስፋፊያ ፕሮጀክት በአገሪቱ ታሪክ የመጀመርያውን ባለ አምስት ፎቅ የመኪና ማቆምያ በ258 ሚሊዮን ብር ገንብቶ በከፊል ለአገልግሎት ክፍት ማድረጉ ይታወሳል፡፡
ከዚህም ባሻገር በቡራዩና በቢሾፍቱ ግዙፍ ሪዞርቶችን ለመገንባት ላይ እንደነበር ይታወቃል፡፡ በመንገድ ግንባታ በአሁኑ ወቅት ከ3 ቢሊየን ብር የማያንሱ ፕሮጀክቶች በእጁ እንደሚገኝ ታውቋል፡፡ በትግራይና አማራ ክልል ከማሃበሬ እስከ ዲማ፣ ከዲማ እስከ ፈየል ዉሀ፣ እንዲሁም ከአዘዞ እስከ ጎርጎራ፣ከድሬዳዋ እስከ ደዋሌ፣ በዚሁ የመንገድ ተቋራጭ የተገቡ ናቸው፡፡ ገመኮን የመንገድ ተቋራጭ እና የሆቴል ፕሮጀክቱን ጨምሮ አቶ ገምሹ በየነ በሥራቸው ከ7ሺ የማያንሱ ጊዝያዊና ቋሚ ሠራተኞችን ያስተዳድራሉ፡፡
አቶ ገምሹ በየነ የኦሮሚያ ክልል የወጣቶችን አመጽ ለማብረድ በተወጠነው የኦሮሚያ የኢኮኖሚ አብዮት ውስጥ ንቁ ተሳትፎ እያደረጉ ከሚገኙ ባለሐብቶች መካከል አንዱ ሲሆኑ የርሳቸው ድርጅት ከሙስና ጋር በተያያዘ ስሙ መነሳቱ የጸረ ሙስና ዘመቻው ውስጥ የኦህዴድ ከፍተኛ ባለሥልጣናት እጅ እንዳለበት አመላካች እንደሆነ የሚያምኑ በርካቶች ናቸው፡፡
Gemshu Beyene- Photo Reporter