የ52ሺህ ቤቶች ግንባታ ማጠናቀቂያ ጊዜ ወደሚቀጥለው ዓመት ተላለፈ

Condos near to Balderasu
Condos near to Balderasu

ዋዜማ ራዲዮ-  ግንባታቸው ቀደም ብለው ከተጀመሩ 171ሺህ የጋራ መኖርያ ቤቶች ዉስጥ የ39ሺ ቤቶች ግንባታ ተጠናቆ ባለፈው ዓመት መጨረሻ ለባለዕድለኞች መተላለፉ ይታወሳል፡፡ ኾኖም ዘንድሮ ግንባታቸው ተገባዶ በዓመቱ መጨረሻ ለነዋሪዎች ይተላለፋሉ ተብሎ እቅድ የተያዘላቸው 52ሺ የሚሆኑ ቤቶች ባሉበት እንዲጸኑ ኾኗል፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ቤቶች ልማት ያጋጠመው ከፍተኛ የበጀት ቀውስ ነው፡፡

እነዚህ ግንባታቸው በአማካይ 48 በመቶ ደርሰው የነበሩ 52ሺህ የ20/80 መርሀግብር ቤቶች ከካቻምና ጀምሮ በግንባታ ላይ የነበሩ ናቸው፡፡ ከነዚህ በተጨማሪ 36ሺ የሚጠጉ ቤቶች ዘንድሮ በተለያዩ ክፍለከተሞች ግንባታ ላይ ነበሩ፡፡ ኾኖም የብዙዎቹ አፈጻጸም ከ20 በመቶ እምብዛምም ከፍ ያለ አልነበረም፡፡ አሁን ባሉበት እንዲረጉ ወይም የግንባታ ፍጻሚያቸው እንዲቆይ የተደረጉት 52ሺ ቤቶች ከ80 በመቶ በላይ ግንባታቸው ገፍቶ እንዳይሄድ ነው የተወሰነው፡፡ ይህም የኾነው ለተቋራጮች የሚከፈልና ቤቶቹን ሊያስጨርስ የሚችል በቂ ገንዘብ ባለመኖሩ ነው ተብሏል፡፡

በዚህም ምክንያት በያዝነው በጀት ዓመት ይጠናቀቃሉ ተብሎ እቅድ ከተያዘላቸው 52ሺ ቤቶች ከፊሎቹን እንኳ ለማስጨረስ የሚያበቃ በጀት እንደሌለ ታውቋል፡፡ ይህንንም ተከትሎ ቤቶች ልማት ተቋራጮችን በጉዳዩ ላይ ጠርቶ ለማናገር ቀጠሮ መያዙ ተነግሯል፡፡ “ኮንትራክተሮች የሚገነቡት ሕንጻ ከ80 በመቶ በላይ ከፍ እንዳይል ቁጥጥር አድርጉ ተብለናል” ይላል ዋዜማ ያናገረችው አንድ የቤቶች ልማት ሠራተኛ፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ለነርሱ የሚከፈል ገንዘብ የለም የሚል ነው፡፡ አንዳንድ ተቋራጮች ቤቶቹን በራሳቸው አቅም በፍጥነት ገንብተው ክፍያ እየጠየቁ ስለሆነ ይህን ለመቆጣጠር ነው ቤቶች ልማት ለተቆጣጣሪዎች መመሪያውን ያስተላለፈው ተብሏል፡፡

ላለፉት ሦስት ወራት በተቋራጮችና በአስገንቢው የቤቶች ልማት መካከል ከፍተኛ ዉዝግብ ተነስቶ እንደነበር መዘገባችን ይታወሳል፡፡ የዉዝግቡ መነሻ ደግሞ ክፍያ ወቅቱን ጠብቆ እየተከፈለን አይደለም የሚል ነው፡፡ 

ምንም እንኳ የክፍያ ሥርዓቱ በየተወሰነ ምዕራፍ የተቋራጮች አፈጻጸምና የደረሱበት የግንባታ ደረጃ እየታየ የሚለቀቅ የነበረ ቢኾንም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን ይህ ሲሆን አልታየም፡፡ በዚህም የተነሳ ተቋራጮች ብዙዎቹ ሥራ ያቆሙ ሲሆን አንዳንዶች ለሠራተኛ የሚከፍሉት ገንዘብ በማጣታቸው ለከፍተኛ ችግር መጋለጣቸው ሲዘገብ ቆይቷል፡፡

ጠንካራ የፋይናንስ አቅም የነበራቸው ተቋራጮች ግን የመንግሥትን ክፍያ ሳይጠብቁ ሕንጻዎቹን በፍጥነት ሠርተው ገንዘብ መጠባበቅን ይመርጡ ነበር፡፡ ይህም የሚያደርጉት ሠራተኞችንና ማሽነሪዎቻቸውን በየጊዜው ወደተለያየ የግንባታ ክልል በማጓጓዝ የሚወጣን ወጪ ለመቀነስ በሚል የሎጂስቲክ ዉሳኔ ነበር፡፡ ኾኖም አሁን ለፈጸሙት ግንባታ ማግኘት የነበረባቸው ክፍያ ከሚገባው በላይ በመዘግየቱ ያልተጠበቀ ቀውስ አጋጥሟቸዋል ተብሏል፡፡ አንዳንዶቹም ቤቶች ልማትን ለመክሰስ በዝግጅት ላይ እንደሆኑም ተሰምቷል፡፡

“እኔ የማውቃቸው ተቋራጮች ለግንበኛ እንኳ የሚከፍሉት ገንዘብ በማጣታቸው ስልክ አጥፍተው ጠፍተዋል፡፡ የተፈጠረው ነገር ግራ የሚያጋባ ነው፡፡ መንግሥት ችግር የለብኝም ይላል፡፡ እንደኔ ግን ኃይለኛ ችግር ዉስጥ የገባ ይመስለኛል” ይላል በግንባታ ቁጥጥር ዘርፍ የተሰማራ አንድ ባለሞያ፡፡

አንዳንድ ተቋራጮች እንደሚናገሩት የጋራ መኖርያ ቤቶችን በተቀመጠው የጥራት ደረጃ መገንባት አትራፊ አያደርግም፡፡ ኾኖም በቤቶች ልማት ተሳትፎ የሚያደርጉ ተቋራጮች ሌሎች በመንግሥት የሚወጡ ጨረታዎችን ለማሸነፍ ሰፊ እድል ስለሚከፍትላቸው ብቻ ነው በሥራው የሚቆዩት፡፡

ሌላው የዉዝግብ ምክንያት ኾኖ የቆየው የብረት ግዢ ከአገር ዉስጥ ብቻ እንዲፈጸም መወሰኑ ነው፡፡ ምንም እንኳ ግዢውን የሚፈጽመው የከተማ ልማት ቢሮ ቢኾንም ከጥራት ጋር በተያያዘ ግን ጥያቄ መነሳቱ አልቀረም፡፡ ዋዜማ ያነጋገረችው አንድ የደረጃ አንድ ተቋራጭ ኢንጂነር “ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የአገር ዉስጥ ብረት እንድንጠቀም በመገደዳችን ሥራውን ለማቋረጥ እያሰብን ነው” ይላል፡፡ ምክንያቱን ሲያብራራም ቀደም ብሎ ከቱርክ የሚገባው ብረት ከፍተኛ ጥራት ያለውና አስተማማኝ ነበር፡፡ አሁን በአገር ዉስጥ ብረት ገንቡ እያሉን ነው፡፡ የአገር ዉስጡን ብረት ደጋግመመሽ ስታጥፈው የመሰበር ምልክት ታይበታለሽ፡፡ የገነባሁት ሕንጻ ኋላ ቢፈርስ ተጠያቂ የምሆነው እኔ ነኝ፤ ማንም መንግሥትን የሚወቅስ አይኖርም፡፡ ስለዚህ ቢቀርብንስ እስከማለት ደርሰናል፡፡” ይላል፡፡

“መንግስት በየዓመቱ ለቤቶች ልማት በቢሊዮን የሚቆጠር ብር ድጎማ ያደርጋል፡፡ የግንባታ ቦታዉን ከሊዝ ነጻ ከማቅረብ ጀምሮ በአካባቢው ለሰፈሩ ነዋሪዎች ካሳ በመስጠት፣ ብረት ከዉጭ አገር ሲገባ ከቀረጥ ነጻ እንዲቀርብ በማድረግ፣ ከፍተኛ ገቢ ያጣል፡፡ በሺህ የሚቆጠሩ ሰራተኞች ለዚህ ፕሮጀክት ሲሰማሩ የአበልና የትራንሰፖርት ክፍያን ይፈጽማል፡፡ የዉሀ፣ መንገድና መብራት መሠረተ ልማት መዘርጋት በራሱ ብዙ ቢሊዮን ብር ማፍሰስ ይጠይቃል፡፡ እነዚህ ወጪዎች ሁሉ ወደሚቆጥበው ነዋሪ ቢተላለፉ የአንድ መኝታ ቤት ዋጋ ወደ 2 ሚሊዮን ብር ሊጠጋ ይችል ነበር” ይላል ይኸው ተቆጣጣሪ መሐንዲስ፡፡

“መንግሥት ጫናው በዝቶበታል፡፡ አቅሙ ደግሞ ዉስን ነው፡፡ ለአንድ ሚሊዮን ተመዝጋቢ ቤት ሠርቶ ማስረከብ ያደጉ አገሮችም የሚችሉት ጉዳይ አይደለም፤ አዲስ መፍትሄ የስፈልጋል” ሲል ሐሳቡን ይሰጣል፡፡ እንደርሱ አመለካከት መፍትሄው ለዉጭ ሪልስቴት ገንቢዎች መሬት በነጻ በመስጠት ግዙፍ የመኖርያ መንደሮችን እንዲፈጥሩ ማድረግ ነው፤ የመንግሥት ሚና የኪራይ ቤቶችን አይነት የቁጠባ ቤቶችን በብዛት ገንብቶ የመፍትሄው አካል መሆን ነው እንጂ ሁሉንም እኔው እፈታዋለሁ ማለት የለበትም” ይላል፡፡

ለቤት ልማት የሚዉለው የብረት ግዢ በራሱ ዉዝግብ ያስነሳ ሌላ ጉዳይ እንደሆነ ይነገራል፡፡ ዋንኛው የዉዝግቡ መነሾ ለቤቶች ልማት የሚውለው ብረት ከዉጭ አገር መገዛት አለበት ወይስ የአገር ዉስጥ አምራቾች ሙሉ በሙሉ ተጠቃሚ ይሁኑ የሚለው ነው፡፡ የአገር ዉስጥ ብረት አምራቾች እኛ እያመረትነው ብረት ስለምን ከዉጭ ይገባል ሲሉ ይጠይቃሉ፡፡ ይህን ጥያቄያቸውን በመንተራስ መንግሥት ከአንድ አመት በፊት ለነርሱ የሚያደላ ዉሳኔን አስተላልፎ ነበር፡፡

አገር ዉስጥ ብረት በማምረት የሚታወቁት ኩባንያዎች በቁጥር ጥቂት ሲሆኑ ስቲሊ አር ኤም አይ፣ ሲ ኤንድ ኢ ብራዘርስ፣ እና ኢስት ስቲል ዋንኞቹ ናቸው፡፡ መንግሥት ለቤቶች ልማት ብቻ በየዓመቱ ከ3ቢሊዮን ብር በላይ የሚያወጣ ብረት ግዢን ይፈጽማል፡፡ እነዚህ ሦሰት ድርጅቶች ደግሞ ብቸኛ ተጫራቾች ኾነው ይቀርባሉ፡፡ ይህም የኾነው ከአንድ አመት በፊት በፋይናንስና ትብብር ሚኒስትር በተጻፈ ደብዳቤ የብረትና የሴራሚክ ግዢዎች ከአገር ዉስጥ አምራቾች ብቻ እንዲፈጸም በመታዘዙ ነው፡፡

የብረት አስመጪዎች በበኩላቸው ለጠቅላይ ሚኒስትር ቢሮና ለደኅንነት መስሪያ ቤት ኃላፊ ለአቶ ጌታቸው አሰፋ ጭምር ግልባጭ ባደረጉት የተቃውሞ ደብዳቤ የአገር ዉስጥ አምራቾች የዚህ ልዩ መብት ተጠቃሚ መሆን እንደሌለባቸው ተሟግተዋል፡፡ ሙግታቸው ለማጠናከርም በርካታ ነጥቦችን አንስተው ተከራክረዋል፡፡

ለምሳሌ የአገር ዉስጥ ብረት አምራቾች ጥሬ እቃውን በዉጭ ምንዛሬ ስለሚያስገቡና ምንም እሴት ሳይጨምሩ ምርት ስለሚያመርቱ የዉጭ ምንዛሬን በማዳን ረገድ ጉልህ ልዩነት እንደማያመጡ አዉስተዋል፡፡ ጥራቱ ዝቅ ያለ ምርት እንደሚመረት ከጠቀሱ በኋላ በዋጋ ደረጃ ግን ከቱርክና ከቻይና ከሚመጣው ብረት ከፍ ያለ ዋጋ እንደሚጠይቁ ያስረዳሉ፡፡ በዓለም ገበያ የብረት ዋጋ ከፍ ያለ ቅናሽ እያሳየ ባለበት ወቅት የአገር ዉስጥ አምራጮች በጨረታ የሚያቀርቡት ዋጋ ከዚህ በተቃራኒው ነው ይላሉ፡፡

ሳምንታዊው ፎርቹን ጋዜጣ ከስድስት ወራት በፊት በጉዳዩ ዙርያ በጻፈው አንድ ዘገባ ቤቶች ልማት ለአንድ ኪሎ ግራም ብረት 18 ብር ገደማ በመክፈል ግዢ እንደፈጸመ ያትታል፡፡ 220ሺ ቶን ብረት ከአገር ዉስጥ አምራቾች ለመግዛት በወቅቱ 3 ቢሊዮን ሰባት መቶ ሺህ ብር ወጪ እንደተደረገ ይገልጻል፡፡ ይህን የብረት መጠን በጊዜው በአለማቀፍ ገበያ ግዢ ቢፈጸም ኖሮ አንድ ቢሊዮን አምስት መቶ ሺህ ብር በሚሆን ወጪ ብቻ አገር ዉስጥ ማድረስ ይቻል ነበር ብለው የብረት አስመጪዎች እንደተከራከሩም አስነብቧል፡፡

መንግሥት ቤት ፈላጊዎች 40 በመቶ እንዲቆጥቡ በማበረታታት ቀሪውን ገንዘብ ከንግድ ባንክ በቦንድ የተሰበሰበ ገንዘብ በማምጣት ለቤት ግንባታ ያውላል፡፡

መንግሥት ባለፈው ዓመት መጨረሻ ላስተላለፋቸው 39ሺህ የሚጠጉ ቤቶች ግንባታ 8 ቢሊዮን ብር ፣ ለመሠረተ ልማት ግንባታ ደግሞ 9 ቢሊዮን ብር፣ በድምሩ 17 ቢሊዮን ብር ወጪ ማድረጉን ይናገራል፡፡

በአዲስ አበባ ወደ 9 መቶ ሺህ የሚጠጉ ነዋሪዎች በ10/90፣ በ20/80 እና በ40/60 መርሀ ግብሮች ቤት ለማግኘት ተመዝግበው በቁጠባ ላይ ቆይተዋል፡፡ ከነዚህ ዉስጥ በ10/90 ለተመዘገቡ ዜጎች 19ሺህ ቤቶች የተላለፉ ሲሆን የተገነቡት ቤቶች ቁጥር ግን ከሚቆጥቡት ዜጎች ቁጥር በላይ ኾኖ በመገኘቱ ሁሉም ተመዝጋቢዎች የቤት እድለኞች ለመሆን ችለዋል፡፡ በዚህም የተነሳ 3ሺህ የሚኾኑ የ10/90 ቤቶች ተርፈዋል፡፡ እነዚህን ቤቶች መንግሥት ከቀበሌ ቤት በልማት ለሚነሱ ዜጎች በኪራይ መልክ ለመስጠት እቅድ አለው፡፡ ይህ ካልሆነም  በመኖርያ እጦት ለሚሰቃዩ የ2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት መምህራን በኪራይ መልክ ሊያስተላልፋቸው እንደሚችል ይገመታል፡፡

በ20/80 መርሀግብር ባለፉት 11 ዓመታት ተገንብተው ለነዋሪዎች የተላለፉት ቤቶች ቁጥር ከ170ሺህ አይበልጥም፡፡ መንግሥት እስከዛሬ በሄደበት ፍጥነት ቤቶችን መገንባት ቢቀጥል ለሁሉም ተመዝጋቢዎች ቤት ገንብቶ ለመጨረስ 52 ዓመታትን ይወስድበታል፡፡