Photo credit- PM office

ዋዜማ- የኢትዮጵያ ዋነኛ አበዳሪ፣ ቻይና ፣ በአውሮፓውያኑ አቆጣጠር እስከ 2024 ድረስ መክፈል የሚጠበቅባትን ግማሽ ቢሊየን ዶላር የኢትዮጵያን ዕዳ መክፈያ ጊዜ አራዘመች።

ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ኢትዮጵያ አባልነቷ ተቀባይነት ባገኘበት የደቡብ አፍሪካው የጆሀንስበርግ የብሪክስ ጉባኤ ላይ ከቻይናው ፕሬዝዳንት ቪ ጂንፒንግ ጋር በነበራቸው ውይይት ነበር የብድር እፎይታው ይፋ የተደረገው። ሆኖም በወቅቱ ስለ ብድር እፎይታው እንጂ ፣ሀገሪቱ ከምን ያክል ብድሯ እፎይታን እንዳገኘች ግን አልተገለጸም ነበር ።

ዋዜማ በዚህ ዙርያ ባደረገችው ማጣራት ከቻይና የተራዘመላት ብድር ወደ 500 ሚሊየን የአሜሪካ ዶላር አካባቢ እንደሆነ ከምንጮቿ መረዳት ችላለች። በጉዳዩ አስተያየታቸውን የጠየቅናቸው እና ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉት ምንጫችን ፣ መክፈያ ጊዜው የተራዘመው የቻይና ብድር ቤይጂንግ ለኢትዮጵያ ከሰጠችው ብድር አንጻር አነስተኛ ቢሆንም ኢትዮጵያ 

በየአመቱ እየከፈለች ካለው ብድር አንጻር ጥሩ የሚባል እፎይታ ስለሆነ በአግባቡ መጠቀም ከተቻለ ለኢኮኖሚው ትንሽም ቢሆን እፎይታ ነው ብለዋል።

ላለፉት አመታት ሀገሪቱ በአማካይ እስከ ሁለት ቢሊየን የአሜሪካ ዶላር በየአመቱ ለብድር ክፍያ ታወጣለች። ከዚህ አንጻር ሲታይ ከቻይና የተገኘው እፎይታ ኢትዮጵያ በአመት ከምትከፍለው ብድር ሩቡን ያክል ይሆናል። 

የገንዘብ ሚኒስቴር በዚህ አመት ያወጣው የመጨረሻው የመንግስትን የእዳ ሁኔታ በሚተነትነው ሰነድ ላይ ፣ የኢትዮጵያ የውጭ ብድር 28 ቢሊየን የአሜሪካ ዶላር መሆኑን ይጠቅሳል። ከዚህ ውስጥ ከ13 ቢሊየን ዶላር በላይ የሚሆነው ከቻይና የተገኘ ብድር እንደሆነ ይታመናል። ቤጂንግ የተጠቀሰውን የኢትዮጵያን ብድር መክፈያ ያራዘመችውም ኢትዮጵያ ከአበዳሪዎቿ ጋር እያደረገች ያለው የእዳ ሽግሽግ ውይይት እስኪጠናቀቅ ፋታ ለመስጠት መሆኑም መነገሩ ይታወሳል። የቻይና ብድር ወለዱ ከሌሎች አበዳሪዎች ከፍ ያለ በመሆኑ ጫና ፈጣሪ መሆኑ ይነገራለ።

ከቅርብ አመታት ወዲህ የኢትዮጵያ እዳ የመክፈል ከፍተኛ ጫና ውስጥ ወድቃለች። የእዳ መክፈል አቅምን የሚለኩ አለማቀፍ ኩባንያዎችም የሀገሪቱን ቁመና ዝቅተኛ ደረጃ ሰጥተውት ቆይተዋል። በሰሜኑ ጦርነት ሳቢያ ሀገሪቱ ከአለም አቀፍ አበዳሪዎች የምታገኘው ፋይናንስ መቋረጡና የወጪ ንግድም በሚፈለገው ልክ አለማደጉ ከፍተኛ ጫና ውስጥ ለመግባቷ በምክንያትነት የሚጠቀስ ነው።

ኢትዮጵያ በቅርብ ወራት ውስጥ የእዳ ማሸጋሸጊያ ተደርጎላት ተጨማሪ ብድር የማታገኝ ከሆነ በተለይ የፈረንጆቹ 2024 ከባድ የእዳ ክፍያ ጫና ውስጥ የምትገባበት አመት ሊሆን እንደሚችል ተሰግቷል። 

ቀጣዩ የፈረንጆቹ አመት ኢትዮጵያ እስካሁን ስትከፍለው ከነበረው መደበኛ ብድር ባሻገር በፈንጆቹ 2014 በዩሮ ቦንድ የተበደረችውና የአስር አመት እድሜ ያለው አንድ ቢሊየን ዩሮ ሙሉው የሚመለስበት አመትም በመሆኑ ጫናው ከፍ ይላል።

ኢትዮጵያ ለአበዳሪዎቿ የጠየቀችው የእዳ ሽግሽግ መዘግየቱን ስትገልጽ ቆይታለች። ከዚህም በተጨማሪ ሀገሪቱ ለሁለተኛው “የሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ” ለአበዳሪዎች የ12 ቢሊየን ዶላር ብድር መጠየቋ የሚታወስ ነው። 

የአለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም (አይ ኤም ኤፍ ) የኢትዮጵያን እዳ ሽግሽግ ጉዳይ ለመጨረስ የሀገሪቱ አበዳሪዎች የመክፈያ ጊዜዋን እንደሚያራዝሙ ቃል የገቡበትን ሰነድ እንዲሰጡ መጠየቁም ይታወቃል። [ዋዜማ]