ዋዜማ ራዲዮ- የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በመሬት እና መሬት ነክ አገልግሎት ላይ ጥሎት ከነበረው እገዳ መካከል፣ በኮንዶሚኒየም እና ንግድ ቤቶች ላይ የጣለውን የይዞታ ካርታ ህትመት እገዳን በማንሳት አገልግሎት እንዲጀመር አዘዘ።


የከተማ አስተዳድሩ ካቢኔ ካቢኔ ከነሐሴ 7 ቀን 2013 ዓ.ም. ጀምሮ ላልተወሰነ ጊዜ አግዶት የቆየውን የመሬትና ይዞታ ነክ አገልግሎቶች በቅርቡ እንደሚያስጀምር ከጥቂት ሳምንታት በፊት መገለጹ ይታወሳል፡፡


በዚህ መሰረት የከተማ አስተዳድሩ መሬት ልማትና አስተዳደር ቢሮ ኃላፊ አቶ ጀማል አልይ ፣ ጥር 2 ቀን 2014 ዓ.ም ለሁሉም ክፍለ ከተሞች በፃፉት ደብዳቤ የከንቲባ ፅህፈት ቤት የጋራ መኖሪያ እና ንግድ ቤት የይዞታ ማረጋገጫ ካርታ ህትመት ላይ ጥሎት የነበረውን ዕግድ ማንሳቱን አስታውሰው ፣ ክፍላተ ከተሞቹ አገልግሎት መስጠት እንዲጀምሩ መመርያ መስጠታቸውን ዋዜማ ያገኘቸው ሰነድ ያሳያል፡፡


ሐላፊው የግብይት ስርዓቱና ልማት መስተጓጎል እንደሌለበት በመጥቀስ ለ 11 ክፍለ ከተሞች የተጻፈው ድብዳቤ የጋራ መኖሪያ ቤትና ንግድ ቤቶች ይዞታ ማረጋገጫ ህትመት የእዳ ማጣራት አገልግሎት እገዳ መነሳቱን ገልጸዋል፡፡


በተጨማሪም ቀሪ እግዶች በቅርቡ እንደሚነሱ የተገለጸ ሲሆን ከተማ አስተዳድሩ በጥቂት ቀናት ውስጥ የህገወጥ የካርታ ድርጊቶች ተጋላጭነትን ያስቀራል የተባለለትን በልዩ ሁኔታ የተዘጋጀ አገልግሎት እንደሚጀምር ተናግረዋል።

የቢሮ ሃላፊው በታህሳስ 2014ዓ.ም መጨረሻ አካባቢ በሰጡት መግለጫ ያላግባብ በየክፍላተ ከተሞች ተሠራጭተው የሚገኙ ካርታዎች ለሕገወጥ ወረራ ተጋላጭ እንዳይሆኑ 472 ሺሕ ካርታዎች ተለይተው መሰብሰባቸውንና ካርታዎቹ መምከናቸውን መናገራቸው ይታወሳል፡፡ [ዋዜማ ራዲዮ]