ዋዜማ- የኢትዮ ጃዝ ሙዚቀኛው ሙላቱ አስታጥቄ የስንብት አልበሙን ለአድማጮቹ እነሆ ብሏል። የሙላቱ የወትሮ አድማጮች በመላው አለም ያሉ የጃዝ ወዳጆች እንደመሆናቸው የሙላቱ አልበም መውጣትም ከሀገሩ ይልቅ በባህር ማዶ ሁነኛ ማድመቂያ ሆኖ ሰንብቷል። 

“ሙላቱ ፕሌይስ ሙላቱ” የአልበሙ መጠሪያ ነው። ይህ አልበም ለ81 አመት ባለፀጋው ሙላቱ አስታጥቄ የመጨረሻው አልበሙ እንደሆነ የቅርብ ወዳጆቹ እየተናገሩ ነው። በእንግሊዝ የአልበሙ ይፋ መደረግን ተከትሎ በነበረ ዝግጅት ላይም የሙላቱ የረጅም ዘመን የሙዚቃ ስኬትን ወዳጆቹና የጃዝ ቤተሰቦች በስስትና በኩራት አክብረውታል። 

አዲሱ አልበም ሙላቱ በህይወት ዘመኑ ከሰራቸውን ሙዚቃዎች የተመረጡ አስራ አንድ ሙዚቃዎችን አሻሽሎና አዳምቆ ያቀረበበት ነው። ሙላቱ አዘውትሮ በሚጎበኘውና ብዙ ታዳሚዎች ባፈራበት በለንደን የረጅም ዓመታት የሙዚቃ ጉዞውን ያከበረ የስንብት ትርዒት አቅርቧል። ትርዒቱ የአዲሱን አልበሙን መውጣት ተከትሎም የተደረገ ነው። 

መክሊት ሀደሮ በጨቅላ ዕድሜዋ ወደ ሀገረ አሜሪካ በስደት የወጣች ድምፃዊት ናት። የመጣችው በርከት ያለ ኢትዮጵያዊ ወደ ሚኖርበት ዋሽንግተን ዲሲ የነበረ ቢሆንም ቤተሰቦቿ ገጠራማ ወደሆነው አይዋ ግዛት ሄደው ለመኖር ተገደዱ። 

ባደገችበት ከተማ ለአውቶቡስ ተሳፋሪዎች ሳይቀር ካልዘፈንኩላችሁ ትል የነበረችው መክሊት በማለዳው የሙዚቃ ተሰጥዖዋን ገፍታበት አለማቀፍ ዕውቅና የተቸራት ድምፃዊና የሙዚቃ ሃያሲ ለመሆን በቅታለች። በአሜሪካ ሚዲያዎች አዝውትራ የምትቀርበው መክሊት ከሶስት መቶ በላይ ጣቢያዎችን ባቀፈው በብሄራዊው የራዲዮ ጣቢያዎች ትስስር  NPR የሙዚቃ ጉዳዮች ዘጋቢ በመሆንም ፕሮግራሞችን ታቀርባለች። 

አዲሱ የሙዚቃ አልበሟ “A Piece of Infinity” ከቀደሙት ሙዚቃዎቿ በተለየ ፍፁም ኢትዮጵያዊ ማንነቶችን የሚያስተዋውቅ ነው። ከእንግሊዘኛ በተጨማሪ አማርኛን ጨምሮ በአራት ቋንቋዎች አዲሱን አልበሟን ተጫውታለች። ከተለያዩ የሀገሪቱ የማህበረሰብ ክፍሎች የተውጣጡ ስልቶችና ዜማዎች በጃዝና በሌሎች ቅንብሮች ተዋዝተው የቀረቡበትም ነው። 

እንደሙላቱ ሁሉ የመክሊትም ሙዚቃ በአብላጫው ኢትዮጵያዊ ባልሆነው አድማጭ ዘንድ የበለጠ የሚደመጡ፣ ሽልማትና ክብር ይዘው የሚመጡ ይመስላሉ። [ዋዜማ]