ዋዜማ- በሰሜን ኢትዮጵያ ውስጥ ካሉት ግዙፍ የጤና ተቋማት አንዱ የሆነው ዓይደር ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ለኹለት ዓመት ከዘለቀው የሰሜን ጦርነት በኋላም ከገጠመው ከፍተኛ ችግር ማገገም ተስኖታል። በተለይም፣ የመድኅኒት እና የህክምና ቁሳቁስ ከፍተኛ እጥረት እና የጤና ባለሙያዎችን ጨምሮ የሆስፒታሉ  ሠራተኞች ከደመወዝ ጋር በተያያዘ ወደ መሀል አገር እና ወደ ውጭ አገራት እየተሰደዱ እንደሚገኙ ዋዜማ ያሰባሰበቻቸው መረጃዎች ያሳያሉ።

በመቀሌ የሚገኘው የዓይደር አጠቃላይ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል፣ በክልሉ የሚገኙ ኹሉም ጤና ጣቢያዎች እና ሆስፒታሎች ከአቅማቸው በላይ ለሚገጥማቸው የህክምና ችግር ታካሚዎቻቸውን የሚልኩበት እንደመሆኑ፣ ለበርካታ ሰዎች የህክምና አገልግሎት መስጠት ቢኖርበትም፣ ከጊዜ ወደ ጊዜ አገልግሎት መስጠት መቸገሩን ዋዜማ ተገንዝባለች።

የዓይደር ሆስፒታል የሕዝብ ግንኙነት አስተባባሪ ብርሃነ ገበረ ሚካኤል፣ ሆስፒታሉ በሰሜን ኢትዮጵያ ሰፊ አገልግሎት ሲሰጥ የቆየ ቢሆንም፣ አሁን ላይ በመድኅኒት እና በላብራቶሪ ቁሳቁሶች የግብዓት እጥረት የተነሳ ትልቅ ችግር ስላጋጠመው፣ ኹሉንም አገልግሎት ፈላጊዎች ለማስተናገድ መቸገሩን ለዋዜማ ተናግረዋል።

ሆስፒታሉ በተለይ ከጦርነቱ በፊት በዋናነት በትግራይ ክልል ላለው ማኅበረሰብ ግልጋሎት ቢሰጥም ከአማራ፣ ከአፋር፣ ከመሀል አገር እንዲሁም አልፎ አልፎ ከኤርትራ ጭምር ለሚመጡ ታካሚዎች አገልግሎት የሚሰጥ ተቋም እንደነበርም አስታውሰዋል። ሆኖም አሁን ላይ በግብዓት እጥረት እና ትላልቅ የህክምና ማሽኖቹ በደረሰባቸው ብልሽት ምክንያት ውስን አገልግሎት ብቻ እየሰጠ እንደሚገኝ ተናግረዋል።

“ታካሚዎች በትንሹም በትልቁም የህክምና አገልግሎት እንዲያገኙ ወደ ግል የጤና ተቋማት ነው የሚላኩት” ያሉት አስተባባሪው፣ ሁኔታው ከጦርነቱ በኋላ ለተቋሙ ሠራተኞች እና በሆስፒታሉ ውስጥ ትምህርታቸውን ለሚከታተሉ የመቀሌ ዩንቨርሲቲ የህክምና ተማሪዎች ሳይቀር አስቸጋሪ መሆኑን ገልጸዋል።

ይህም የጤና ባለሙያዎች በመድኅኒት እና በግብዓት እጥረት ምክንያት በሙሉ አቅማቸው መስራት እንዳልቻሉ እና በዚሁ ችግር የተነሳ ተማሪዎቹ በተግባር የተደገፈ ትምህርታቸውን በተገቢው ሁኔታ መከታተል አስቸጋሪ መሆኑን አክለው ተናግረዋል።

ከደመወዝ ጋር በተገናኘ እና በሁኔታዎች ተስፋ በመቁረጥ ወደ መሀል አገርና ወደ ውጭ የሚሰደዱ የሆስፒታሉ ሐኪሞች፣ ነርሶች እና የፋርማሲ ባለሙያዎች መኖራቸውንም ጠቁመዋል። “ምን ያህል  ሠራተኞች ተቋሙን ለቀው እንደወጡ ለጊዜው መረጃው እጄ ላይ ባይኖርም፣ በየጊዜው ግን በተለይ የጤና ባለሙያዎቹ እየተሰደዱ ነው” ሲሉም ለዋዜማ ተናግረዋል።

ብርሃነ አክለውም፣ የኤም አር አይ እና  የሲቲ ስካን ህክምና መስጪያ ማሽኖች በመበላሸታቸው አገልግሎቱ ሙሉ ለሙሉ መቋረጡን ገልጸው፣ ከእነዚህ ችግሮች ባለፈም በማንኛውም የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል ማግኘት የማይከብዱ የደም ምርመራ አገልግሎቶች አለመኖራቸውን አመልክተዋል። የመድሃኒት እጥረት ችግሩ የጎላ መሆኑን ጠቅሰውም፣ ለድንገተኛ ታማሚዎች የሚሆኑ መድሃኒቶች ሳይቀር ከፍተኛ እጥረት መኖሩን ገልጸዋል።

የዓይደር ሆስፒታል ላብራቶሪ ክፍል ምክትል አስተባባሪ ዳዊት ሰሚል በበኩላቸው፣ ከጦርነቱ በፊት እስከ 95 ዓይነት የምርመራ አገልግሎቶች ይሰጡ እንደነበር ጠቅሰው፣ አሁን ላይ ከ30 በታች የምርመራ አገልግሎት ብቻ እንደሚሰጥ ጠቅሰዋል። መሰረታዊ የሚባሉ ምርመራዎች ሳይቀር ተቋርጠዋል ያሉት ዳዊት፣ ላለብን የግብዓት ዕጥረት የፌደራሉን የመድኅኒት አቅራቢ ተቋም በተደጋጋሚ ብንጠይቅም ችግሩ ሊፈታ አልቻለም ብለዋል።

ለተቋሙ ሠራተኞች ደመወዝ መከፈል የተጀመረው ከፕሪቶሪያው የሰላም ስምምነት ጊዜ ጀምሮ ነው ያሉት ዳዊት፣ ከሰላም ስምምነቱ በፊት የ17 ወር ደመወዝ እንዳልተከፈላቸው እና ጦርነቱ ከተጀመረ አንስቶም የትርፍ ጊዜ ክፍያ አለመኖሩን ለዋዜማ አስረድተዋል። ለመሰረታዊ የምርመራ አገልግሎት የሚጠቅሙ ማሽኖች ሥራ ማቆማቸውን እና ችግሩ መች እንደሚፈታ እንደማያውቁ ጭምር ዳዊት ገልጸዋል።

“በሆስፒታሉ ውስጥ የላብራቶሪ አግልግሎት ከሌለ የህክምና አገልግሎት መስጠት አይቻልም” ያሉት ዳዊት፣ ችግሩ እንዲፈታ ለፌደራሉ የግብዓትና የመድኅኒት አቅርቦት ተቋም በተደጋጋሚ አቤት ብንልም መፍትሄ አልተገኘም ብለዋል። የተሟላ የህክምና አገልግሎት ባለመኖሩም ታካሚዎች በአንድ ቀን ማግኘት የነበረባቸውን አግልግሎት እስከ ሳምንት ወይም አንድ ወር ድረስ ሊጠብቁ እንደሚችሉ ገልጸዋል። ይህም ታካሚዎችን ለተባባሰ የጤና ቀውስ እና ላልተፈለገ ወቺ እንደሚዳርጋቸው ጠቅሰዋል።

የሆስፒታሉ ፋርማሲ ክፍል ምክትል መሪ ዳናዊት ገብረ መስቀል በበኩላቸው፣ ለሆስፒታሉ የሚቀርበው መድኅኒት ለተጠቃሚዎች በቂ አለመሆኑን እና ለተወሰኑ ታካሚዎች ከደረሰ በኋላ እንደሚያልቅም ለዋዜማ ተናግረዋል። ሆኖም ከቀደሙ ጊዜ አንጻር አሁን የተወሰነ መሻሻል አለ ያሉት ዳናዊት፣ በኹሉም የህክምና ዘርፎች ላይ የመድኅኒት እጥረቱ እንዳለ ፤ ይህም ሊከሰት የቻለው የፌደራሉ የመድኅኒት አቅራቢ ተቋም በጠየቅነው ልክ ስለማያቀርብልን ነው ብለውናል። 

ዋዜማ በሆስፒታሉ ተገኝታ የህክምና አገልግሎት ለማግኘት ሲጠባበቁ የነበሩ ተገልጋዮችን ባነጋገረችበት ወቅት፣ በተለይ መድኅኒት ሆስፒታል ውስጥ የለም እየተባሉ መቸገራቸውን እና ከውጭ ፋርማሲዎች በውድ ዋጋ እንደሚገዙ ታካሚዎቹ ተናግረዋል። ይሁን እንጂ ታካሚዎች የሆስፒታሉ መድኅኒት በሕገ-ወጥ መንገድ ለግል መድኅኒት ቤቶች ተላልፎ ይሰጣል በሚል ያቀረቡትን ቅሬታ፣ ዳናዊት የተሳሳተ ነው ሲሉ አጣጥለውታል።

“የግል መድኅኒት ቤቶች ፍላጎቱን ስለሚያውቁ በራሳቸው ገንዘብ ስለሚያቀርቡ ነው በሆስፒታል የሌለ መድኅኒት እነርሱ ዘንድ የሚገኘው”  ሲሉም የታካሚዎቹን ቅሬታ “መሰረት የሌለው” ብለውታል። ታካሚዎች ግን ጓንት ሳይቀር ከውጪ ግዙ እንደሚባሉ ጠቅሰው፣ አቅም የሌላቸው ህመምተኞች የማይታከሙበት ደረጃ ላይ ደርሰዋልም ሲሉ የችግሩን ጥልቀት ተናግረዋል።  [ዋዜማ]