[ዋዜማ ራዲዮ] በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የኢ-ፍትሀዊ የብሄር ስብጥር አለባቸው የተባሉ ቁልፍ ተቋማት ላይ የማስካከያ ውሳኔ እንዲያሳልፉ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ጥናት ቀረበ።

ምክትል ከንቲባ ታከለ ኡማ ከመጡ ጀምሮ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ስር ባሉ ተቋማት ያለ የብሄር ስብጥር ጉዳይ አጨቃጫቂ ሆኖ መቆየቱ የሚታወቅ ነው። ይህ ጉዳይ በተለይም በኦሮሞ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኦዴፓ) እና በአማራ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (አዴፓ) መካከል መቃቃርን ሲፈጥር እንደነበር የሚታወስ ነው።

በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ስር ባሉ ቀልፍ ተቋማት ስር ያለው የሰው ሀይል ስብጥር ኢ ፍትሀዊ ነው ተብሎ በመታመኑ ነው ለጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ለማስተካከያ ውሳኔ የቀረበው።


ዋዜማ ራዲዮ እንዳገኘችው መረጃ ከሆነ በከተማ አስተዳደሩ ኢ ፍትሀዊ የሰው ሀይል ስብጥር በዝቶባቸዋል ከተባሉ ተቋማት ውስጥ
የከተማው መብራት አገልግሎት ፣ የውሀና ፍሳሽ ባለስልጣን ፣ መንገዶች ባለስልጣን ፣ቤቶች ልማት ፣ መሬት አስተዳደር ፣ ወሳኝ ኩነት ፣ የአካባቢ ጥበቃ እንዲሁም የወንዞች ዳርቻ ልማትና የሰላምና ጸጥታ ተቋም ይገኝበታል።

በእነዚህ ተቋማት ውስጥም የኦሮሞ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ ( ኦዴፓ) አባላት ያልተገባ ድርሻ ማግኘታቸው ተምኖበታል። ይህም ብቻ ሳይሆን ኦዴፓ በነዚህ ተቋማት ውስጥ የሙያ ብቃት ሳይሆን አባልነትን ብቻ መስፈርት አድርጎ አባላቱን አከማችቷል ተብሏል። በዚህ ላይ የማስተካከያ ውሳኔን እንዲያሳልፉ ሰነድ የቀረበላቸው ጠቅላይ ሚኒስትሩ ውሳኔ ይሰጡበታል ተብሎ ይጠበቃል። [ዋዜማ ራዲዮ]