Billene Seyoum, PM office Press Secretary, PHOTO CREDIT- Michael Tewelde

ዋዜማ ራዲዮ- የኢትዮጵያ መንግስት መረጃን ለህዝብ በማቅረብና ተአማኒ በመሆን ረገድ ያለብኝን ችግር ይፈታል ያለውን የተግባቦት ሰነድ አዘጋጅቶ ወደ ስራ ገብቷል።


በጠቅላይ ሚንስትሩ ፅህፈት ቤት የተዘጋጀውና ዋዜማ ራዲዮ ያገኘችው “የኢፌዴሪ የተግባቦት ሰነድ” ከተለያዩ የመንግስት አካላት፣ ለጠቅላይ ሚንስትሩ ፅህፈት ቤት ቅርብ በሆኑ ጋዜጠኞች፣ በመረጃና ደህንነት ተቋሙና በክልል መስተዳድር አካላት ሀሳብ የተሰጠበት እንደሆነ በመግቢያው ላይ ያትታል።


የሰነዱ ግብ መንግስት ከለውጡ ማግስት ጀምሮ ያከናወናቸውንና እያከናወነ ያለውን በጎ ተግባር ህዝቡ በሚገባ እንዲረዳና ድጋፍ እንዲሰጥ ለማስቻል ነው። እስካሁን በነበረው የመረጃ ፍሰት ከፍተኛ የሆነ የተቋማት የቅንጅት ችግር ነበረብን ብሏል።
አሁን በጠቅላይ ሚንስትሩ ፅህፈት ቤት የፕሬስ ሰክረታሪያት የፌደራሉ መንግስት ተቋማትና መንግስታዊ መዋቅሮችን የሚመራ አዲስ አደረጃጀት ተዘርግቷል።

ቀድሞ የነበረው የመንግስት ኮምኒኬሽን ጉዳዮች ፅ/ቤት መፍረሱ በመንግስት የተግባብቦት ስራ ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ ማሳደሩንም ስነዱ ይገልጻል።

እያንዳንዱ የመንግስት ተቋም እንደየ ስፋቱ ተጠሪ የኮምኒኬሽን ግብረኀይል እንዲያቋቁም ስነዱ ያዛል።
የግብረኀይሉ እስከ ስድስት የሚደርሱ ንዑስ ቡድኖች ይኖሩታል ። እነዚህ ቡድኖች – ስትራተጂክ ኮሙኒኬሽንስ ፣ የመገናኛ ብዙሀን ግንኙነት አስተባባሪ ፣ የውጪ ግንኙነት፣ ዲጂታል ኮሙኒኬሽንስ፣ የውስጥ ግንኙነት ና የማኅበራዊ ቅስቀሳ ቡድን ተብለው የሚዋቀሩ ናቸው።


መንግስታዊውን የመረጃ ፍሰት ለማቀናጀት ሲባል እያንዳንዱ መስሪያቤት የሁለት ሳምንት የስራ ዕቅዱን ወደ ጠቅላይ ሚንስትሩ ቢሮ ልኮ ማስፀደቅ ይጠበቅበታል።


“የመገናኛ ብዙሀን ትኩረት የሚያገኙ ከመንግስት የሚመጡ ማናቸውም ዜናዎች በእቅድ ሰነዱ ውስጥ መካተት እና ለጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት ቀድመው መጋራት አለባቸው “ ሲል ይመክራል ሰነዱ።

የመረጃ ሰራተኞቹ በፊናቸው የሚኒስትሮች መልእክቶች ፣ ንግግሮች ፣ ጋዜጣዊ መግለጫዎች እና ጉብኝቶች ፣ ሚኒስትሮች የተሳተፉባቸው ቃለ-ምልልሶች ወይም ርእሰ አንቀጾች ፣ የመገናኛ ብዙሀን ሽፋን የሚያገኙ ስብሰባዎች ፣ ዓለም አቀፍ ስብሰባዎችን ለጠቅላይ ሚንስትሩ ፅህፈትቤት ያሳውቃሉ ።


ከመንግስት ተቋማት ውጪ ያሉ መረጃዎችንና ክንውኖችንም መንግስታዊ ባልሆኑ ድርጅቶች የተሰራ የስታትስቲክስ/መረጃ ልቀቶች ፣ መንግስታዊ ባልሆኑ ድርጅቶች የተዘጋጁ ሪፖርቶች፣ የመገናኛ ብዙሃንን ትኩረት የሚስቡ የፍርድ ቤት ውሳኔዎችን መከታተል የነዚሁ የመረጃ ግብረሀይል ስራተኞች ድርሻ ነው።

በየተቋማቱ የሚወከሉ የመረጃ ሐላፊዎች አለቆቻቸው አልያም የሚመለከተው የክፍል ሐላፊ ከጋዜጠኞች ጋር ቃለምልልስ የሚያደርግ ከሆነ ጥያቄ ያቀረበው ሚዲያና ጋዜጠኛ፣ የውይይቱ ጭብጥ እንዲሁም በውይይቱ የተካፈሉ ሌሎች አካላት ካሉ በቅፅ ተዘርዝረው ሪፖርት ይደረጋሉ።


የማህበራዊ ሚዲያን አንገብጋቢ አስፈላጊነት ያብራራው የሰነዱ ክፍል ደግሞ
“ ክንውኖችን ለመከታተል፣ ልዩ ልዩ መረጃዎችን ለመሰብሰብ እና ዋነኛ ተጽዕኖ አሳዳሪዎችን ለመለየት ያስችለናል፡፡ መደበኛ የዜና አውታሮችን ከሚከታተሉ ተተኳሪ አካላት ባለፈ መልእክቶቻችንን በቀጥታ በማድረስ ተጽዕኖ ለማሳደር ዕድልን ያመቻችልናል “ ሲል ይጀምራል።

የሕዝቡ የልብ ትርታ ምን እንደ ሆነ ለመገንዘብ እና ወቅታዊ ጉዳዮችን ለመከታተል ማህበራዊ ሚዲያ መጠቀም አስፈላጊ መሆኑን ይገልፅና ትኩረት ሳቢ እና ከተቋማችን ጋር ግንኙነት ያላቸውን ‘የሶስተኛ ወገን ይዘት’ ማጋራት ያለውን ጠቀሜታ ይጠቁማል።


“ ጥብቅ እና የተወሰኑ ሐላፊዎች ብቻ ሊያውቋቸው የሚገቡ መረጃዎችን ወይም ከወንጀለኛ፣ ከሽብርተኛ ወይም ከስለላ አካላት በእናንተ ወይም በባልደረቦቻችሁ ላይ አደጋ ሊያስከትሉ የሚችሉ መረጃዎችን ይፋ አታውጡ” ሲልም ይመክራል።


የመንግስት ባለስልጣናት እና ሲቪል ሰራተኞች ማህበራዊ ሚዲያ መጠቀም እንደማይከለከሉ ይሁንና የያዙትን ሐላፊነት የሚፃረርና የፖለቲካ ወገንተኝነትን የሚያንፀባርቅ መረጃ ከማጋራት እንዲቆጠቡ ይላል ይህ የመንግስት የተግባቦት ሰነድ።
መረጃዎች በከፍተኛ ባለስልጣናትና በየተቋሞቹ ማህበራዊ ገፆች ቢሰራጩ ጠቃሚ መሆኑን ያብራራል።


በቀውስ ግዜ የሚኖር የመረጃ ማቀናጀትና ማዕከላዊ በሆነ መንገድ መረጃን ማሰራጨት ተገቢ መሆኑን ዘርዝሯል። [ዋዜማ ራዲዮ]