በኢሬቻው ዕልቂት ያኮረፉና ማንነታቸውን ያልገለፁ ህቡዕ የከተማዋ ወጣቶች ዝግጅቱን ለማስተጓጎል ዛቻ ያዘለ ወረቀት በትነዋል

ዋዜማ ራዲዮ- በሳምንቱ መጨረሻ በቢሾፍቱ ከተማ ኩሪፍቱ ሪዞርት የተዘጋጀው የዳንኪራ ትዕይንት በሺ የሚቆጠሩ ሰዎች ይታደሙታል ተብሎ ይጠበቃል።  ለሁለት ቀናት የሚካሄድ ትዕይንት ከውጪ ሀገር ድረሰ የመጡ የሙዚቃ አጫዋቾች ዲጄ የተካተቱበት ሲሆን የመግቢያ ዋጋው እስከ ስድስት መቶ ብር ነው።

ኮረንቲ በሚል ስያሜ የሚጠራው ይህ የዳንኪራ ትዕይንት በቢሾፍቱ የኢሬቻ በዓል ዕልቂት ወዲህ በርካታ ሰዎች የሚገኙበት ክንውን ነው።

የዝግጅቱ ማስታወቂያ በመገናኛ ብዙሀን በተደጋጋሚ መተላለፉን ተከትሎ በኢሬቻው ዕልቂት ያኮረፉና ማንነታቸውን ያልገለፁ ህቡዕ የከተማዋ ወጣቶች ዝግጅቱን ለማስተጓጎል ዛቻ ያዘለ ወረቀት በከተማይቱ መበተናቸውንና ለወጣቶች ጥሪ መተላለፉን የዋዜማ ሪፖርተር ከአካባቢው ያገኘችው መረጃ ያመለክታል።
“የወንድሞቻችን ደም ሳይደርቅ በቢሾፍቱ ገዳዮቻችን የዳንስ ፕሮግራም ስላዘጋጁ የከተማዋ ወጣቶች እርምጃ ለመውሰድ እንድትዘጋጁ”  ይላል ማክስኞና ሀሞስ ዕለት የተበተነ በኦሮምኛ የተፃፈ ወረቀት።
የዳንኪራ ፕሮግራሙ ከጀርባ ሆኖ አዘጋጅቶታል የተባለው  ጆርካ ኢቨንትስ “በገዥው ፓርቲ ባለስልጣናት ልጆች የተቋቋመ ነው” የሚለው ወሬ በከተማዋ በስፋት መናፈሱ የአካባቢው ወጣቶች ዝግጅቱን በጥላቻ እንዲመለከቱት ሳያደርግ እንደልቀረ የአካባቢው ነዋሪዎች ይናገራሉ።
በህወሀት ታጋዮቹ አቶ ስብሀት ነጋ፣ ታጋይና ድምፃዊ ኢያሱ በርሄ ልጆች (ተከስተ ስብሀትና ረዊና ኢያሱን ጨምሮ ሌሎችም) ያሉበት ጆርካ ኢቨንትስ በሀገሪቱ ዋና ዋና የሚባሉ የሙዚቃ ኮንሰርቶችን በማዘጋጀት ይታወቃል። ጆርካ ኢቨንትስ በተመሳሳይ በመቀሌም ትልቅ ኮንሰርት አዘጋጅቶ ታዳሚውን ጋብዟል።
በስልክ ያነጋገርናቸው የቢሾፍቱ ማዘጋጃ ቤት የሰራ ሀላፊ ቅዳሜና እሁድ የሚደረገው ዝግጅት ከከተማው አስተዳደር ጋር ምንም ግንኙነት የሌለውና በኩሪፍቱ ሪዞርት የተዘጋጀ መሆኑን ይሁንና በርካታ ሰዎች ይታደሙበታል በመባሉ የከተማው ፖሊስና የኮማንድ ፖስቱ በጋራ ልዩ የፀጥታ ጥበቃ ለማድረግ መዘጋጀታቸውን ገልፀዋል።
ሀገሪቱ በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ስር ባለችበት በዚህ ወቅት በተለይም ደም መፋሰስ በደረሰበት አካባቢ ይህን ትዕይንት ለማዘጋጀት ፈቃድ እንዴት እንደተገኘ ለጆርካ ኢቨንትስ አባላት  ላቀረብንላቸው ጥያቄ ምላሽ አልስጡንም።