Andreas Eshete
Andreas Eshete

ዋዜማ ራዲዮ- ከኢትዮጵያ አንጋፋ ምሁራን አንዱ የሆኑትና በተለያየ ሀላፊነት መንግስትን ያገለገሉት ፕሮፌሰር አንድርያስ እሸቴ በፅኑ ታመው በሆስፒታል አልጋ ላይ እንደሚገኙ የዋዜማ ምንጮች ተናግረዋል።
ፕሮፌስር አንድርያስ ስሞኑን ያረፉት የወዳጃቸው የዶር ገብሩ መርሻ ሞት አልተነገራቸውም።
በተማሪ ንቅናቄ ንቁ ተሳታፊ የነበሩትና በብሄር መብት ጉዳይ ተሟጋችነታቸው የሚታወቁት ፕሮፌሰር አንድርያስ የአንድ ልጅ አባት ናቸው። ከሽግግር ዘመን ጀምሮ ለገዥው ፓርቲ ህገ መንግስት በማርቀቅና በማማከር ከፍተኛ ተሳትፎ ያደረጉት ፕሮፌሰር አንድርያስ የአዲስ አበባ ዩንቨርሲቲ መምህርና ፕሬዝዳንትም ሆነው አገልግለዋል። በቅርብ አመታትም የሟቹ ጠቅላይ ሚንስትር መለስ ዜናዊ አማካሪ ሆነው ሲሰሩ ነበር።
በፖለቲካ አቋማቸው ቀላል የማይባል ውግዘት የሚቀርብባቸው ፕሮፌሰር አንድርያስ ላመኑበት አላማ በመቆም ፅናታቸው ምስጋናም አላጡም። በምሁራዊ ብቃታቸውም አንቱታን አግኝተዋል። ፕሮፌሰር አንድርያስ ከዚህ ቀደም ከገጠማቸው ብርቱ ህመም ውጪ ሀገር ሄደው በመታከም ማገገማቸው ይታወሳል። አብዝተው ሲጋራ በማጨስ የሚታወቁት አንድርያስ ያለፉትን ወራት በተደጋጋሚ ሲታመሙ እንደነበርና ያሁኑ ግን ጠንከር ያለ መሆኑን የቅርብ ወዳጆቻቸው ይናገራሉ።