ከአዘጋጁ፡ ይህ ዜና አዳዲስ መረጃ ትክሎበታል፣ በስተ መጨረሻው ላይ ተመልክቷል።

ዋዜማ ራዲዮ- 2018-03-11-PHOTO-00000054የታዋቂው አትሌትና ባለሀብት ኃይሌ ገብረስላሴ ንብረት የሆነ  ሪዞርት በአስቸኳያ ጊዜ አዋጁ ስበብ በኮማንድ ፖስቱ እንዲዘጋ መደረጉን የዋዜማ ሪፖርተሮች አረጋግጠዋል።
በኦሮምያ ክልል ሱሉልታ ከተማ የሚገኘው ያያ ሪዞርት ( Yaya Africa Athletics Village)  ባለፈው ሳምንት የተጠራውን የሶስት ቀናት የስራ ማቆም አድማ ተከትሎ አገልግሎት በማቋረጡ ሳቢያ የኮማንድ ፖስቱ ተቆጣጣሪዎች እንዳሸጉትና እስከ ቅዳሜ ምሽት ድረስ ተዘግቶ እንደነበር ተመልክተናል።

ድርጅቱን ለማስከፈት አትሌት ኃይሌ ገብረስላሴ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ውይይት እያደረገ እንደነበርም የደረሰን መረጃ ያመለክታል።
ይህ ጉዳይ በእንጥልጥል ባለበት ወቅት ኃይሌና ሌሎች ለመንግስት ቅርብ የሆኑ የሀገር ሽማግሌዎች የኢትዮጵያ ቀውስ በሽምግልና እንዲፈታ ሙከራ እያደረጉ የነበረበት ወቅት ነው።
ኃይሌ በመንግስት መገናኛ ብዙሀን ቀርቦ የስራ ማቆም አድማ በሰለጠነው አለም ታይቶ የማይታወቅ የተቃውሞ ስልት ነው ሲል በማጣጣሉ ከፍተኛ የህዝብ ተቃውሞ እየቀረበበት ስንብቷል።
የተቃውሞው ምክንያት ስራ አጥነት ነው ያለው ኃይሌ ችግሩን በሰላማዊ መንገድ እንዲፈታ መክሯል።
ኃይሌ በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች ትላልቅ የንግድ ተቋማትን ገንብቶ የሚንቀሳቀስ ሲሆን በፖለቲካ ጉዳዮች ላይ የሚሰጣቸው ብስለት የሚጎድላቸው አስተያየቶቹ አትሌቱ ለዓመታት የተጎናፀፈውን ክብር የማይመጥኑ በመሆናቸው ይተቻል።

የተጨመረ- ይህ ዜና ይፋ ከሆነ በኋላ ኃይሌ ገብረሥላሴ በድጋሚ ድርጅቱ በአድማ ተባባሪነት እንደማይዘጋ ቃል በመግባትና በመፈረም፣ የንግድ ድርጅቱ እንዲከፈትለት መወሰኑ  ተናግሯል።
ሪዞርቱ በአድማው ወቅት የተዘጋው ካልታወቁ አካላት በመጣ ማስፈራሪያ መሆኑን የገለፀው ኃይሌ መንግስት ጥበቃ ካላደረገልን ስራችን ለማከናወን እንቸገራለን ሲል ለሸገር ራዲዮ ተናግሯል።