derg officialsዋዜማ ራዲዮ- ከጥቂት ዓመታት በፊት በይቅርታ የተፈቱት የደርግ ከፍተኛ ባለሥልጣናት ባሳለፍነው ሳምንት ከጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ዳሳለኝ ቢሮ በመገኘት ለአንድ ሰዓት የቆየ ዉይይት ማካሄዳቸው ተሰምቷል፡፡ ዉይይቱ በዋናነት ያተኮረው ሻምበል ፍቅረሥላሴ ወግደረስ በሊቀመንበርነት በሚመሩት ሰውለሰው የተሰኘ የመረዳጃ ማኅበር የቦታ ጥያቄ ላይ ቢኾንም ከዚያ ባለፈ አንዳንድ ፖለቲካዊና ወቅታዊ ጉዳዮች በዉይይቱ መነሳታቸው ተመልክቷል፡፡

በተለይም አገሪቱ አሁን ያለችበትን ፈታኝ ወቅት በምን መልክ ማለፍ እንደሚቻል፣ የመንግሥታቸውን የአስተዳደር ዘይቤው ምን መምሰል እንዳለበት ከእድሜና ከልምድ በመነሳት የሚሰማቸውን እንዲናገሩ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ከተጋበዙ በኋላ  ጥቅል ምክሮች ኮሎኔል ፍሰሐ ደስታ በኩል ለጠቅላይ ሚኒስትሩ መቅረባቸው ታውቋል፡፡

ሻምበል ፍሰሐ ምን አይነት ምክር እንሰጡ የዋዜማ ምንጮች ማብራራት ባይችሉም ይህ መንግሥት መሠረት ልማት ላይ ያለው ተሳትፎን ማወደሳቸውንና አገራዊ አንድነት ላይም በተመሳሳይ መልኩ መሰራት እንዳለበት እንደሚያምኑ በትህትና መናገራቸውን ገልጠዋል፡፡

የደርግ ባለሥልጣናቱ ለመረዳጃ ማኅበራቸው ያነሱትን የቦታ ጥያቄ ተመርኩዘው ‹‹የመሬት ጥያቄያቸውን  በተመለከተ ከድሪባ ጋር በመሆን መፍትሄ እንፈልግለታለን፣ እናንተ ሥራችሁን ቀጥሉ›› የሚል በጎ ምላሽ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ማግኘታቸው ታውቋል፡፡

ኮሎኔል ፍሰሀ ደስታ በበኩላቸው መንግሥት በልማት ላይ የሄደበትን ርቀትና ቁርጠኝነት ካወደሱ በኋላ አገርን በጋራ ስለመገንባት የሚሰማቸወን አስተያየት ማንጸባረቃቸው ተመልክታል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም የደርግ ባለሥልጣናቱን ሲያሰናብቱ ይህንን በወንድማማችነትና በይቅርባይነት መንፈስ የተደረገውን ዉይይታቸውን በተመለከተ ለሚዲያ ፍጆታ እንዳያዉሉትና እርሳቸው ራሳቸው ጊዜውን ጠብቀው ለሕዝብ ይፋ እንደሚያደርጉት ነግረዋቸዋል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ የደርግ ባለሥልጣናቱን ሲያወያዩ አንድም ሌላ ባለሥልጣን በቢሯቸው አልነበረም ተብሏል፡፡ ደርጎቹ ጠቅላይ ሚኒስትሩን ለማናገር ጥያቄያቸውን ባቀረቡ በአጭር ጊዜ ዉስጥ ወደ ቤተመንግሥት ተጠርተው ፍጹም ቀና በሆነ መልካም መስተንግዶ መወያየት መቻላቸውና ለጥያቄያቸውም በጎ ምላሽ ማግኘታቸው እንዳስገረማቸውና ያልጠበቁት መሆኑን ሻምበል ፍቅረሥላሴ ለወዳጆቻቸው ተናግረዋል፡፡ ሻምበል ፍቅረሥላሴ በአሁኑ ሰዓት አዲሱ ገበያ የእግዜአብሔርአብ ቤተክርስቲያን አቅራቢያ የሚኖሩ ሲሆን እስከአሁንም ከኪራይ ቤት አልወጡም፡፡

ሰው ለ ሰው የተሰኘው የመረዳጃ ማኅበር በቀድሞው የደርግ ባለሥልጣናት የተመሠረተ እድር ሲኾን በከተማዋ እምብርት የራሱን ሕንጻ በመገንባት ገቢ ለማግኘትና አባላቱን ለማገዝ ፍላጎት አለው፡፡