Dr.Birhanu Nega
Dr.Birhanu Nega

ዋዜማ ራዲዮ – የአርበኞች ግንቦት ሰባት አመራሮች ከጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ አህመድ ጋር በአሜሪካ ባደረጉት ሁለት ዙር ዝግ ውይይት ወደ ሀገር ቤት ተመልሰው በሰላማዊ መንገድ በፖለቲካ የሚሳተፉበት ሁኔታ ላይ መስማማታቸው ተሰማ።
አርብ ዕኩለ ለሊት አቅራቢያ በተጠናቀቀው ውይይት ላይ በኤርትራ ያሉ የአርበኞች ግንቦት ሰባት ታጋዮችን በተመለከት እንዲሁም ሀገሪቱ ወደ ፊት ወደ ዴሞክራሲ ሽግግር ለማድረግ በሚረዷት ጉዳዮች ላይ ሰፊ ውይይት መደረጉን በስብሰባው የተካፈሉ ምንጮች ነግረውናል። በቅርቡም ድርጅቱ በኢትዮጵያ በይፋ እንቅስቃሴ እንደሚጀምር ይጠበቃል።

በጉዳዩ ላይ ድርጅቱ ዝርዝር መግለጫ እንደሚያወጣ ይጠበቃል።
የአርበኞች ግንቦት ሰባት ቀድሞ በሀገር ቤት በህቡዕ ይንቀሳቀሱ የነበሩ አባላቱን ወደ ሰላማዊ የፖለቲካ ትግል የማምጣትና የማደራጀት ዕቅድ እንዳለውም ከድርጅቱ የተገኘ መረጃ ያመለክታል።
የድርጅቱ ዋና ፀሀፊ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ሐሙስ እለት ከሚኖሩበት እንግሊዝ ወደ አሜሪካ የመጡ ሲሆን በውይይቱ ላይ ተሳታፊ ነበሩ።

ተጨማሪ ዝርዝር እንደደረሰን እናክልበታለን