1. የጋምቤላ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ጋትሉክ ቱት በታጣቂዎች የተወሰዱ ህፃናትን ለማስለቀቅ የመከላከያ ሰራዊት በታገቱበት ቦታ (ደቡብ ሱዳን) ደርሶ የመጨረሻ እርምጃ ለመውሰድ እየተሰናዳ መሆኑን ለራዲዮ ፋና ተናግረዋል። ህፃናቱ ሙሉ በሙሉ በደህና ወደ ሀገራቸው እንደሚመለሱ በእርግጠኝነት ተናግረዋል። የተወሰዱት ከብቶችም ይመለሳሉ ብለዋል። ገና በሚከናወን (ባላለቀ) ወታደራዊ ተልዕኮ ውጤታማነት ላይ ርዕሰ መስተዳድሩ ያሳዩት እርግጠኝነት ያልተለመደና ቀድሞውኑስ ህፃናት ታግተዋልን የሚያስብል ነው። የጋምቤላው ጥቃት ሀገራዊ የድንበር መደፈርና ብሄራዊ ሀዘን ሆኖ ሳለ የመከላከያ ሰራዊቱን የግዳጅ አፈፃፀም ሲሆን የጦሩ አዛዦች ካልሆነ የፌደራሉ መንግስት ቃል አቀባይ ለምን አልተናገሩትም? 

2. የጋምቤላውን ጥቃት ያደረሱት የሙረሌ ጎሳ ታጣቂዎች መሆናቸውን የኢትዮዽያ መንግስት አስታወቋል። ይሁንና የሙረሌ ጎሳ ጥቃቱ ከደረሰበት የኑዌር መኖሪያ ጋር አይዋሰንም። ስለዚህ በኑዌር አልያም በአኝዋክ ጉሳ መሬት ላይ ካልተሸጋገረ ጥቃቱን ማድረስ አይቻለውም። በነዚህ ጎሳዎች ዘንድ ሙረሌዎች በጠላትነት የሚታዩ ከመሆናቸው አንፃር ተሻግረው ጥቃት አድርሰው መመለሳቸው እንቆቅልሽ ነው። (ካርታውን ይመልከቱ)

Pagak indicator

3. ታጣቂዎቹ  ዘመናዊ መሳሪያ የታጠቁና የወታደር የደንብ ልብስ የለበሱ መሆናቸዉን እማኞች መስክረዋል። አንድ የአርብቶ አደር ታጣቂ የተትረፈረፈ ጥይት የመገናኛ ራዲዮና የነፍስ ወከፍ ዘመናዊ መሳሪያ እንዴት ሊታጠቅ ቻለ የሚለው ምላሽ የሚፈልግ ጥያቄ ነው።

4. በጥቃቱ አልያም በኢትዮዽያ መንግስት ተገደሉ ከተባሉት ውስጥ የዲንቃ ጎሳ አባለት አስከሬን ተገኝቷል። የሙረሌና የዲንቃ ጉሳ አባላት መቼም ተስማምተው በጋራ ተሰልፈው አያውቁም። ታዲያ ዲንቃዎች እዚህ ውስጥ ምን እግር ጣላቸው?

5. ሙረሌዎችን የሚያስተዳድረው ማነው? ፒቦር በተሰኘችው አካባቢ ቦማ ግዛት የከተሙት ሙረሌዎች በቅርቡ የደቡብ ሱዳን መንግስት ጋር እርቅ ባደረገው የዴቪድ ያዉ አማፂ ሚሊሻ የሚተዳደር ነው። አስተዳደሩ በጁባ ካለው የደቡብ ሱዳን መንግስት ትዕዛዝ ተቀብሎ የሚሰራ ነው። አካባቢው መረጋጋት የራቀውና ተደጋጋሚ ግጭቶች ያሉበት ነው። ይህ ቡድን የኑዌር ጎሳ አባል የሆኑትንና የምክትል ፕሬዝዳንትነት መንበር ለመያዝ የሚጠበቁትን ሪክ ማቻርን ክፉኛ የሚቀናቀን ቡድን ነው። የዚህ ቡድን ሚና በጥቃቱ ምን ነበር?

6. የጥቃቱ ፈፃሚዎች ተልዕኮ ምን ነበረ? ጥቃቱ በተፈፀመበት አካባቢ በስብሰባ ላይ የነበሩትንና በመኪና ረጅም መንገድ ለመንቀሳቀስ ዕቅድ የነበራቸውን የደቡብ ሱዳን አማፅያን መሪ መግደል?  ታጣቂዎቹ የመጡት ከብት ለመዝረፍና ልጆችን ለማገት ከሆነ መከላከል ያልሞከረውን የአካባቢውን ህዝብ ለምን ጨፈጨፉት? በቀል ወይስ ሌላ?

ማስታወሻ- ይህን አጭር ጥያቄ በስራ ከሚወዳጁን የደቡብ ሱዳን እህት ራዲዮ ጋር በጋራ የመረጥነው ሲሆን ለታዳሚዎቻችን እንዲስማማ አርታኦት ጨምረንበታል