Photo credit -ECC

ዋዜማ- የኢትዮጵያ ጉምሩክ ኮሚሽን፣ ተገልጋዮቹ በአንድ የባንክ ፍቃድ ከአንድ ጊዜ በላይ ምርት ወደ አገር ቤት እንዳያስገቡም ሆነ ወደ ውጪ እንዳይልኩ ትእዛዝ ማስተላለፉን ይመለከታቸዋል ላላቸው አካላት ከጻፈው ደብዳቤ ዋዜማ መገንዘብ ችላለች።

ኮሚሽኑ እዚኽ ውሳኔ ላይ  የደረስኩት፣ አንዳንድ ላኪዎች እና አስመጪዎች በአንድ የባንክ ፍቃድ በተለያየ ጊዜ ምርቶችን መላክ እና ማስመጣት የሚፈቅደውን ህግ፣ የአገርን ጥቅም በሚያሳጣ እና በሕገ ወጥ መንገድ እየተጠቀሙበት እንደሆነ ስለደረስኩበት ነው እንዳለ ከደብዳቤው ተረድተናል። እስከ አሁን ጥቅም ላይ የነበረው የጉምሩክ ሥርዓት፣ የተገልጋዮችን ሥራ ለማቅለል ሲባል አስመጪዎች እና ላኪዎች በባንክ የተፈቀደላቸውን አንድ የባንክ ፍቃድ ሰነድ በመጠቀም፣ እቃዎችን በተለያዩ ጊዜያት እንዲያስገቡ እና እንዲልኩ ይፈቅዳል።

ስማቸው እንዲገለጽ ያልፈለጉ አንድ የጉምሩክ ኮሚሽን ከፍተኛ ባለሙያ፣ “በአንድ የባንክ ፍቃድ በተለያየ ጊዜ ምርት ማስገባት መፈቀዱ ለብዙ ያልተገቡ አሰራሮች መንገዶችን ከፍቶ ቆይቷል” ሲሉ ለዋዜማ ተናግረዋል። ባለሙያው እንደገለጡት፣ “በአንድ የባንክ ፍቃድ በተለያየ ጊዜ ምርቶችን ማስመጣት መፈቀዱ፣ አስመጪዎች የተፈቀደላቸው የውጭ ምንዛሬ ከሚችለው በላይ ምርቶችን በተለያዩ ጊዜያት እንዲያስገቡ ሁኔታዎችን አመቻችቷል”ም ብለውናል። ባለሙያው ለማሳያነትም በሚል፣ ወደ አገር ውስጥ በገፍ የገቡትን መኪኖች ያነሳሉ።

መንግስት በነዳጅ ለሚሰሩ መኪኖች ባንኮች የውጭ ምንዛሪ እንዳይፈቅዱ ካዘዘ ዓመት ቢያልፍም፣ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ መኪኖቹ ሲገቡ የቆዩት፣ ለእነዚኽ መኪኖች የውጭ ምንዛሬ እንዲከለከል ከመደረጉ በፊት በተገኘ የባንክ ፍቃድ ምክንያት መሆኑንም ጨምረው ያነሳሉ። 

 ዋዜማ እንደተረዳችው ከሆነ፣ በክፍልፋይ ጊዜ በአንድ የባንክ ፍቃድ በተለያዩ ወቅቶች ምርቶችን ማስገባት መፈቀዱ፣ አስመጪዎቹ ባንክ ከፈቀደላቸው የውጭ ምንዛሪ በላይ የሚያወጡ ምርቶችን የማስገባት ዕድሎችን እንደመፍጠሩ፣ በዚኽም ባንኩ ከፈቀደላቸው ውጭ ጥቅም ላይ ያዋሉት ገንዘብ ከጥቁር ገበያ የተገኘ ነው የሚለውን ጥርጣሬ ከማሳደጉ ባለፈ፣ አሰራሩም ሕገ ወጥ ገበያን አበረታቷል የሚል አተያይን በጉምሩክ ኮሚሽኑ በኩል አስይዟል።

  የጉምሩክ ኮሚሽኑ፣ ከኅዳር 10 2016 ዓ.ም. ጀምሮ በአንድ የባንክ ፍቃድ ከአንድ ጊዜ በላይ ምርትን ማስገባት የሚከለክለውን አሰራር እንደሚተገብር ገልጿል። ለኢትዮጵያ ብሄራዊ ባንክ በጻፈው ደብዳቤም፣ የንግድ ባንኮች ፍቃድ ሲሰጡ ይህንኑ ታሳቢ እንዲያደርጉ ማሳሰቡንም ዋዜማ ራዲዮ መረዳት ችላለች።   [ዋዜማ]