addis-condo

  • ዕጣ የሚወጣላቸው ዜጎች ከ90 ሺ እስከ 150 ሺ ብር ጭማሪ ገንዘብ ሊጠየቁ ይችላሉ
  • ዘንድሮ አዲስ የሚጀመር የቤቶች ግንባታ ላይኖር ይችላል

ዋዜማ ራዲዮ- ከተጠናቀቁ ዘለግ ያለ ጊዜን ያስቆጠሩትና በዓይነታቸው የመጀመርያ የሆኑት የ40/60 ቤቶች ጉዳይ ሦስት መንግሥታዊ መሥሪያ ቤቶችን እያወዛገበ ይገኛል፡፡

የኮንስትራክሽንና ልማት ቢሮ፣ የንግድ ባንክና የከንቲባው ጽሕፈት ቤት በጋራ ያቋቋሙት ኮሚቴ የተገነቡት ቤቶች  የሚተላለፉበት አግባብ ምን መምሰል አለበት፣ የክፍያ ስሌቱ መሰላት ያለበት በምን መልኩ ነው፣ በስህተት             የተፈፀመው የዲዛይን ለውጥ ያስከተለው ኪሳራ ማን ይሸከመው በሚሉት ጉዳዮች ላይ ከመግባባት ለመድረስ ተቸግረዋል፡፡ ይህም ሁኔታ ከተጠናቀቁ ዘለግ ያሉ ወራትን የስቆጠሩ 1292 ቤቶች ወደ እጣ ሥነ ሥርዓት እንዳይገቡ እንቅፋት ሆኗል፡፡

ዋዜማ ከንግድ ባንክ ሁነኛ ምንጮች ያገኘችው መረጃ እንደሚያስረዳው ዉዝግቡ የተነሳው አሁን ደቡብ ኮሪያ ለ3ኛ ዲግሪ የተጓዙት አቶ መኩሪያ ኃይሌ በሥልጣናቸው ሳሉ ጀምሮ ሲሆን ጉዳዩ እስካሁንም እልባት አላገኘም፡፡ እርሳቸው ለጉዳዩ የመጨረሻ እልባት ለመስጠት ጫፍ ደርሰው እንደነበር ግን ምንጮች አመላክተዋል፡፡

በኮሚቴው ዉስጥ ተሳትፎ ያላቸው አንድ የባንኩ ባልደረባ እንደገለጹት በሰንጋ ተራ የተገነቡት ቤቶች ሌሎች የከተማዋ ቀበሌዎች ላይ ከሚገነቡት ቤቶች የተለየ መጠንና አቀማመጥ አላቸው፡፡ የመኖርያ ቤቶቹ የሚጀምሩት ከሦስተኛ ፎቅ አንስቶ ሲሆን አንደኛ ፎቅና ሜዛኔን ወለልን ጨምሮ  ለንግድ አገልግሎት እንዲሆኑ ታሳቢ ተደርገው የተገነቡ ናቸው፡፡ ይህ ብቻም ሳይሆን ባለ አንድ፣ ባለ ሁለትና ባለ ሦስት መኝታዎች ያላቸው አቀማመጥና የካሬ ስፋት ከንግድ ባንክ ጋር ዉል የገቡ ደንበኞች ከተረዱትና ከፈጸሙት የካሬ ስምምነት ፍጹም የተለዩ ናቸው፡፡

በዚህ የተነሳ ይህ ዲዛይን ለውጥ ያስከተለውን እዳ ማን መክፍል አለበት የሚለው ዋንኛ የዉዝግብ መነሻ ሆኖ ሰንብቷል፡፡

በንግድ ባንክ ምክትል ኃላፊ የሚመራው የባንኩ ተወካዮች ስብስብ በዚህ ጉዳይ ላይ የያዘው አቋም ለዉል ተቀባይ የሚያደላ ነው፡፡ከደንበኞች ጋር አንድ ጊዜ ዉል በመፈጸሙ የኮንስትራክሽን ሚኒስትር በፈጸመው ስህተትና ከዉሉ ዉጭ ለተገነባ ቤት ደንበኞችን ባለ እዳ ማድረግ ከአሰራር ዉጭ ነው ሲል ተከራክሯል፡፡ የዲዛይን ስሕተት ፈጽሟል የተባለው ደረጃ አንድ አማካሪ የሆነው ኢቲጂ ኮንሰልቲንግና አርክቴክት በበኩሉ ከመስሪያ ቤቱ በተሰጠኝ ስምምነት መሰረት ዲዛይኑ ፀድቆልኝ ነው ንድፉን ሰርቼ ያስረከብኩት ሲል ይከራከራል፡፡

ኢቲጂ አማካሪዎች ሠርቶ ያቀረበው ይህ ዲዛይን ወደ ግንባታ ሲለወጥ የቤቶቹ ስፋት ዉል ከተገባው በተለየ በአማካይ በ40 ስኩዌር ካሬ ያህል ለውጥ  አምጥቷል፡፡ በዚህም መሰረት ለአንድ መኝታ የተመዘገበ ደንበኛ የተዋዋለው ለ55 ስኩዌር ካሬ ቢሆንም የሚረከበው ቤት ወደ 95 ሜትር ካሬ ስፋት እንዳለው ተመልክቷል፡፡ ባለሁለት መኝታ በዉሉ ከተኬደ 75 ካሬ ያህል ብቻ የሚሰፋ ሲሆን የሰንጋ ተራ እድለኛ ይህን ቤት ሲረከብ 115 ካሬ ኾኖ ሊያጋጥመው ይችላል፡፡ 100 ስኩዌር ካሬ ስፋት እንደሚኖረው ይጠበቅ የነበረው  ባለሦስት መኝታም ግንባታው የ27 ካሬ ጭማሪን በማሳየቱ አሁን በ127 ስኩዌር ካሬ ስፋት እንዲኖረው ተደርጎ ነው ግንባታው የተጠናቀቀው፡፡ እነዚህ የካሬ ጭማሪዎች የሚገኙት ቀድመው ተገንብተው በተጠናቀቁት ሳይቶች ላይ ብቻ ነው፡፡

እነዚህ የካሬ ጭማሪዎች በዋጋ ላይ ከፍተኛ ልዩነትን መማጣታቸው አልቀረም፡፡ ይህን የካሬ ጭማሪ ወጪ ማን ይሸፍን የሚለው ነው የመስሪያ ቤቶቹ የዉዝግብ መነሾ፡፡

የከንቲባውን ጽሕፈት ቤት በቤቶች ልማት ጉዳይ የሚወክሉት አቶ አባተ ስጦታው በበኩላቸው በጉዳዩ ላይ ጠንካራ አቋም ይዘው ተከራክረዋል፡፡ እርሳቸው ለኮሚቴው ሲያስረዱ “እንደመታደል ሆኖ የካሬ ማነስ ሳይሆን መስፋት ነው የገጠመን፣ ይህ መልካም ነገር ነው፡፡ የሚሰራ ይሳሳታል፡፡ በበኩሌ እጣ የሚወጣላቸው ነዋሪዎች በካሬው መስፋት ምክንያት ገንዘብ ጨምሩ ብንላቸው ቅር ይሰኛሉ ብዬ አላምንም፡፡ እንዲያዉም ደስተኛ የሚሆኑ ይመስለኛል፡፡ ሰፊ ቤት ለማግኘት አልተዋዋልኩም ብሎ የሚከሰን ነዋሪ ካለ የሚቀጥለውን እጣ ጠብቆ ጠበብ ያለ ቤት መውሰድ ይችላል” ሲሉ ጉዳዩ አሳሳቢ እንዳልሆነ አስረድተዋል፡፡

በንግድ ባንክ ምክትል ኃላፊ በኩል የተያዘው አቋም ግን “ደንበኛን ከዉል ዉጭ ለተፈጸመ ነገር ገንዘብ ጨምር ብሎ ጥፋተኛ ማድረግ እንደ አሰራር አግባብ አይደለም” የሚል ነው፡፡

የአቶ አባተ ስጦታው ሐሳብ ተቀባይት ካገኘ በሰንጋተራና በክራውን የተገነቡ ቤቶች ዕጣ የሚወጣላቸው ዜጎች በዚህ ያልተጠበቀ የካሬ መስፋፋት የተነሳ ከ90 ሺ እስከ 150 ሺ ብር ጭማሪ ገንዘብ ሊጠየቁ ይችላሉ፡፡ ይህ ስሌት በጥሬ እቃ አቅርቦት ምክንያት ሊጨምር የሚችለውን የዋጋ ክለሳ አይጨምርም፡፡ ካፒታል የተሰኘው ሳምንታዊው የእንግሊዝኛ ጋዜጣ ባሳለፍነው እሁድ እንደዘገበው በዋጋ ክለሳው ለእያንዳንዱ ስኩዌር ካሬ 2100 ብር ጭማሪ ሊኖር እንደሚችል የሚጠቁም ዜና አውጥቷል፡፡ በዚህ ስሌት መሠረት 55ካሬ ለሚሰፋ ባለ አንድ መኝታ ወደ 115ሺ ጭማሪ በክለሳው ምክንያት ይኖራል እንደማለት ነው፡፡ በሰንጋተራና በክራውን ሳይቶች ከዉል ዉጭ ለተጨመረ ካሬ 85ሺ ብር የሚጠጋ ክፍያ መጠየቅ ሊኖር ይችላል፡፡ ይህ ስሌት ባለ አንድ መኝታ ጠቅላላ ዋጋን ወደ 300 መቶ ሺ ብር ሊያደርሰው ይችላል ተብሎ ተሰግቷል፡፡

ይህ በእንዲህ እያለ ዘንድሮ አዲስ የሚጀመር የ40/60 ፕሮጀክት መኖሩ አጠያያቂ እንደሆነ ከንግድ ባንክ ምንጮች የተገኘ መረጃ ያመላክታል፡፡ ይህም ከፋይናንስ መድረቅ ጋር የተያያዘ ነው፡፡

 መንግሥት የ40/60 ፕሮጀክቶች እንዲቀጥሉ ከፍተኛ ፍላጎት ያለው እንደሆነ የገለጹት የቤቶች ልማት ኮሚቴ አባልና የባንኩ ባልደረባ  ይህም የሆነው በዚህ ማዕቀፍ ያሉ ነዋሪዎች መቆጠብ የቻሉት ገንዘብ ሌሎች የ20/80 እና የ10/90  ፕሮጀክቶችን ለማስኬድ እጅግ ወሳኝ ስለሆነ ነው ብለዋል፡፡ መንግሥት እስካሁን በዚህ የ40/60 ማዕቀፍ ብቻ ከ15 እስከ 20 ቢሊዮን ብር መሰብሰብ ችሏል፡፡ ይህ ገንዘብ ባይኖር ሌሎች የቤት ልማቶችን ለማስቀጠል ፋይናንስ ለማግኘት አዳጋች ይሆን እንደነበር ያብራራሉ፡፡

በአሁኑ ሰዓት እየተገነቡ የሚገኙ በቁጥር 39ሺ የሚሆኑ የ40/60 ግንባታዎች በተለያዩ ቀበሌዎች የሚገኙ ሲሆን ተቋራጮች “በወቅቱ ገንዘብ እየተለቀቀልን አይደለም” በሚል አብዛኛዎቹ ግንባታዎች እንዲቆሙ ሆነዋል፡፡ ንግድ ባንክ እስካሁን በነበረው ሂደት ደስተኛ ስላይደለ ቤቶቹን የራሱን መሐንዲሶች አሰማርቶ የግንባታ ቁጥጥርና ክትትል እያደረጉ በፍጥነት እንዲገነቡ ፍላጎት እንዳለው ባለሞያው አብራርተዋል፡፡ ባንክ ያወጣው ገንዘብ ቶሎ እንዲመለስለት ይሻል፡፡ ቶሎ ከተመለሰለት ሌሎች ፕሮጀክቶችን ቶሎ መጀመር ይችላል፡፡ የቤቶቹ ግንባታ በተጓተተ ቁጥር ባንኩ ኪሳራ ላይ እየወደቀ ነው፣ ለዚህም ነው በዚህ አመት የሚጀመር አዲስ ፕሮጀክት ላይኖር ይችላል የምለው ሲሉ እኚሁ ግለሰብ ያብራራሉ፡፡

ለቤቶቹ መጓተት ዋናው ምክንያት ምን እንደሆነ የተጠየቁት እኚህ የኮሚቴ አባል መንግሥት በአንድ ድንጋይ ብዙ ወፎችን ለመምታት በማለሙ እንደሆነ ያስረዳሉ፡፡ ባለሞያው እንደሚሉት በ12 ወራት በርካታ ብሎኮችን ጥንቅቅ አድርገው መጨረስ የሚችሉ አገር በቀል ተቋራጮች ቢኖሩንም ግንባታው ላይ እንዲሳተፉ ግን በመንግሥት በኩል አይፈለግም ይላሉ፡፡

“መንግሥት በጥቃቅንና አነስተኛ የተደራጁ ወጣቶችን ተጠቃሚ ማድረግ ይፈልጋል፣ ከቴክኖሎጂ ይልቅ ሰፊ የሰው ኃይል በግንባታው እንዲሳተፍ ፍላጎት አለው፡፡ እቃ የሚያቀርቡት ጥቃቅንና አነስተኛ ድርጅቶች ናቸው፡፡ ገንቢዎቹ በተጭበረበረ ፍቃድ የሚሰሩ ወጣት ልጆች ናቸው፣ ከጥራትና ከቤቶቹ በጊዜ መጠናቀቅ ይልቅ መንግሥትን በብዙ የሚያስጨንቀው ወጣቶቹ ሥራ እንዳይፈቱና የፖለቲካ ችግር እንዳይፈጥሩበት ነው” ሲሉ ሁኔታዉን ያብራራሉ፡፡

40/60 ማዕቀፍ በተዘጋጀበት ዓመት መንግሥት ከፍተኛ የዉጭ ምንዛሬ እጥረት ገጥሞት እንደነበር የተናገሩት የባንኩ ባለሞያ በዉጭ የሚገኙ ኢትዮጵያዉያን ተሳትፎ ማድረጋቸው ችግሩን በጊዝያዊነት ለማቃለል እንደረዳ ያስታውሳሉ፡፡ ያም ሆኖ በመንግሥት በኩል በርካታ ዳያስፖራ አባላትን በዉጭ ምንዛሬ ክፍያ እየፈጸሙ በቤቶች ልማት በስፋት ለማሳተፍ ከፍ ያለ ፍላጎት የነበረ ቢሆንም ይህ እቅድ እምብዛምም አልተሳካም ይላሉ፡፡ በወቅቱ ወጥቶ በነበረ ታሪፍ ለባለ አንድ መኝታ 144 ዶላር፣ ለባለሁለት መኝታ 223 ዶላር፣ ለባለ ሶሰት መኝታ 344 ዶላር በየወሩ መቆጠብ እንደሚኖርባቸው ተተምኖ ነበር፡፡

በ12 የከተማዋ ጥጎች 39ሺ ቤቶች በአሁኑ ሰዓት ግንባታ ላይ እንደሆኑ ይታመናል፡፡ በሰንጋ ተራ 12 ወለሎች ያሏቸው 5 ብሎኮች ይገኛሉ፡፡ በክራውን ሆቴል በ14 ብሎኮች ዉስጥ የታቀፉ 882 ቤቶችን ተገንብተዋል፡፡ እነዚህ ቤቶች ቢበዛ በ8 ሳምንት ጊዜ ዉስጥ ለነዋሪዎቹ ይተላለፋሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡ የቤቶቹን እጣ የሚያወጣውም ንግድ ባንክ እንደሚሆን ሳምንታዊው የሪፖርተር ጋዜጣ በእሁድ እትሙ አስነብቧል፡፡

በቦሌ አያት የሚገኘው የ40/60 ፕሮጀክት ትልቁ የ40/60 ፕሮጀክት የሚባለው ሲሆን 11ሺ 319 ቤቶችን በዉስጡ ይዟል፡፡ የግንባታ ደረጃዉ ግን ከ50 በመቶ ብዙም ፈቅ አላለም፡፡

በመሐል ከተማው የሚገኝ ክፍት ቦታዎች እንደልብ አለመገኘት ፕሮጀክቱ ከታቀደለት ዉጭ በማስፋፊያ ክልሎች ለመገንባት ተገዷል፡፡ የሰንጋተራ፣ የቦሌ ቡልቡላ፣ የገርጂ፣ የ24 ቀበሌ፣ የእህል ንግድ፣ የሕንጻ አቅራቢ ሳይቶች ካልሆኑ በስተቀር አሁን እየተገነቡ የሚገኙ የ40/60 ፕሮጀክቶች ወጣ ባሉ የማስፋፊያ ዞኖች የተጀመሩ ናቸው፡፡ ከዚህ በኋላ በቀጣይ ዓመት ግንባታቸው ለሚጀመሩ ቤቶች እስካሁን የመስተዳደሩ መሬት ዝግጅት ቦታ ምደባ አላካሄደም፡፡ ምናልባት የመልሶ ማልማት ቦታዎችን ተከትሎ የ40/60 ቤቶች ልማት ማካሄጃ ክፍት ቦታዎች በሂደት ሊገኙ ይችላሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡

አሁን በሰንጋተራና በክራውን የተጠናቀቀቱት የ40/60 ቤቶች ባለ 12 ፎቅ ይሁኑ እንጂ አዲስ የሚገነቡትና ወደፊት የሚገነቡት ቤቶች ግን መልከ ብዙ እንደሚሆኑ ተመልክቷል፡፡ ባለ 16፣ ባለ 18 እና ባለ 20 ወለል የሚይዙት ሁለት ምድር ቤት (ቤዝመንት) እንዲኖራቸው በኢቲጂ ኮንሰልቲንግ ንድፍ የተሰራ ሲሆን ባለ 24 ወለል ያላቸው ደግሞ ሦስት ወለል ወደታች (ቤዝመንት) እንዲኖራቸው ተደርገው የሚገነቡ ይሆናሉ፡፡ ወደላይ ወለል መጨመር የተፈለገው ከተማዋ ወደ ጎን መለጠጥ የምትችለውን ያህል ተጉዛ ቦታ በመታጣቱ ነው፡፡

ከአመታት በፊት በተካሄደ ምዝገባ 160ሺ ከሚጠጉ ቤት ፈላጊዎች ዉል ፈጽመው ለሚነቡ ቤቶች ፍላጎት ያሳዩ ሲሆን ከነዚህ ወስጥ 4 በመቶ የሚሆኑት ብቻ ናቸው ለአንድ መኝታ ቤት የተመዘገቡት፡፡ 45 በመቶ የሚሆኑት ባለ ሁለት መኝታን ሲመርጡ 51 በመቶ የሚሆኑት ግን ምርጫቸው ባለ 3 መኝታን አድርገዋል፡፡ 150 የሚሆኑ ተቋራጮች በግንባታ እየተሳተፉ ቆይተዋል፡፡

መንግሥት አሁን ባለው የግንባታ ፍጥነት ቤቶቹን መገንባት ከቀጠለ ዉል ለፈጸሙ ዜጎች ቤቶቹን ሙሉ በሙሉ አጠናቆ ለመጨረስ 12 ዓመታትን ሊወስድበት ይችላል፡፡