ዋዜማ ራዲዮ- መንግስት የብር በዶላር ምንዛሪ ተመንን በዝግታ ለማዳከም ከለጋሾች ጋር ተስማምቶ ነበር። ይሁን እንጂ የሀገሪቱ ኢኮኖሚ በገጠመው ፈተና ብር በራሱ ጊዜ ለጋሾች ካስቀመጡት ተመን ኣአሽቆልቁሏል። የለጋሾች ጫናና ሀገራዊ የኣኢኮኖሚ ፈተናው ለጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ አስተዳደር ራስ ምታት ሆኖ መሰንበቱ አይቀሬ ይመስላል። መንግስት የኢኮኖሚውን መሰረታዊ ችግር ከመፍታት ይልቅ የአለማቀፍ የገንዘብ ተቋማትን ትእዛዝ መተግበር ላይ አተኩሯል በሚል ትችት እየበዛበት ነው። በዚህ ዘገባ ዘለግ ያለ ዘገባ የፋይናንስ ዘርፉ የገጠመውን ፈተና ዋዜማ ራዲዮ ከተለያዩ የመረጃ ምንጮች ጠይቃለች አንብቡት


የኢትዮጵያ ብር የውጭ ምንዛሬ ተመን ለዚህ አመት ታቅዶ ከነበረውም በላይ እየተዳከመ እንደሆነ ዋዜማ ራዲዮ ሰምታለች።የኢትዮጵያ መንግስት ከአለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም : አይኤምኤፍ : እና የአለም ባንክ ከፍተኛ የሆነ ድጋፍ እንዲያገኝ ያስቻለውን የሶስት አመት የሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ ሲያዘጋጅ አንዱ ተቀብሎት ፈርሞበት የነበረው ቅድመ ሁኔታ የሀገሪቱን መገበያያ ብር የውጭ ምንዛሬ ተመን በፍጥነት እንዲያዳክም ፣ በጊዜ ሂደት ደግሞ የብር የውጭ ምንዛሬ ተመን በገበያ እንዲወሰን ማድረግ የሚለውን ነው።


ዋዜማ ራዲዮ ከታማኝ ምንጮቿ እንደሰማችው መንግስት በዚህ አመት የብር የምንዛሬ ተመንን እያዳከመ ከእነ አይኤምኤፍ ጋር በተስማማው መሰረት  አንድ የአሜሪካን ዶላር በ36 ብር እንዲመነዘር ነበር አቅዶ ሲሰራ የነበረው። አሁን ላይም አንድ የአሜሪካ ዶላርን ባንኮች የሚገዙበት  ይፋዊ ዋጋም እዚሁ ዋጋ ላይ ደርሷል።

ይህን ዘገባ እስከሰራንበት ነሀሴ 22 2012 አ.ም የአንድ አሜሪካን ዶላር የባንኮች መግዣ ዋጋ 36.1083 ብር ሆኗል። ባንኮች አንድ የአሜሪካ ዶላርን የሚሸጡበት ዋጋም በተመሳሳይ ቀን 36.8304 ብር ነበር።


ብር ከሌሎች ሀገራት የመገበያያ ገንዘቦች አንጻርም እንዲሁ እየተዳከመ ነው።የኢትዮጵያ ብር በዚህ ሂደት ውስጥ ሲያልፍ ከህዳር 3 2012 አ.ም ጀምሮ በ22 በመቶ እንዲዳከም ተደርጎ ነው። ያኔ የአንድ አሜሪካን ዶላር ዋጋ 29.4966 ብር ነበር። እለት ጀምሮ የአንድ የአሜሪካን ዶላር ዋጋ በየቀኑ ከፍ ሲል ከአስር ሳንቲም በላይ ዝቅ ሲል ደግሞ አራት ሳንቲም እየጨመረ ብር በፍጥነት እየተዳከመ የአንድ ዶላር ዋጋ በይፋዊ ገበያ ከስድስት ብር በላይ ጭማሬን አሳይቷል።


 መንግስት በ2003 እና 2010 አ.ም የብር የውጭ ምንዛሬ ተመንን በአንድ ቀን ካዳከመ በሁዋላ የአሁኑ መልኩን ቀይሮ የተደረገ የብር ማዳከም አሰራር ነው። እስከ አሁን ዘጠኝ ወር የወሰደው የአሁኑ የምንዛሬ ተመን ማሻሻያም መንግስት ከእነ አይኤምኤፍ ጋር የገባው የኢኮኖሚ ማሻሻያ እንደሆነ በተደጋጋሚ የተገለጸ ሲሆን : ይህን ጨምሮ ይተገበራሉ ለተባሉ የተለያዩ የኢኮኖሚ ማሻሻያዎችም የኢትዮጵያ መንግስት 10 ቢሊየን ዶላር ከተለያዩ አበዳሪ ተቋማት ቃል ተገብቶለት ገንዘቡ በሂደት እየተለቀቀለት እንደሆነም ተገልጿል።


ሆኖም ብርን በዚህ ደረጃ የማዳከሙ ግብ በታሰበው ልክ ከመሆኑ በተቃራኒ ለሀገሪቱ ኢኮኖሚ እያተረፈ ያለው ከፍተኛ የዋጋ ግሽበት ነው። የምንዛሬ ተመንን ማዳከም በዚህ ደረጃ እንዲፈጸም የተፈለገው ምርትን ወደ ውጭ ሀገር የሚልኩ ባለሀብቶችን በማረታታት ሀገሪቱ የውጭ ምንዛሬ ግኝቷ እንዲጨምር ለማድረግ በማለም ነው።
የዚህ አመት የኢትዮጵያ የወጭ ንግድ ግኝት በተወሰኑ መቶ ሚሊየን ዶላሮች ጨምሮ ሶስት ቢሊየን የአሜሪካን ዶላርን ቢያልፍም ይህ የሆነው ግን በምንዛሬ ተመን ላይ በታየው የአሰራር ለውጥ ሳይሆን ወርቅን በመሰሉ ለውጭ በቀረቡ ምርቶች ያልታሰበ የዋጋ ጭማሬ እንደሆነ ተገልጿል። እርግጥ መንግስት ከእነ አይ ኤም ኤፍ ጋር ውል ከገባ በሁዋላ የኮቪድ 19 ወረርሽኝ በመከሰቱ በወጪ ንግድ ላይ የታሰበው ለውጥ መጥቷል ባይባልም አሁን እየሆነ ያለው ብርን የማዳከሙ ነገር በዋጋ ግሽበት ላይ ያመጣው መናር አመዝኗል።


ኢትዮጵያ በአመዛኙ ምርት የምታስገባ ሀገር እንደመሆኗ የብር ምንዛሬ ማሽቆልቆል ያስከተለው ብቸኛ ነገር የዋጋ ግሽበት ሆኗል። የዋጋ ግሽበት ጉዳይ በኮሮና ቫይረስ ብቻ የሚሳበብ እንዳልሆነ የሚያስረዱ ባለሙያዎች አሉ። ምክንያቱም ኢትዮጵያ ውስጥ ቫይረሱ ከመግባቱ መጋቢት ወር በፊትም ቢሆን በየወሩ የሚመዘገበው የዋጋ ግሽበት ከ20 በመቶ በላይ ነበር። በሀምሌ ወር የዋጋ ግሽበቱ 21.6 በመቶ የነበረ ሲሆን በዚሁ ወር የምግብ የዋጋ ግሽበት 23.1 በመቶ ሆኗል። አሁን ላይ የኮሮና ወረርሽኝ ካመጣው የኢኮኖሚ ጫና ባለፈ የዋጋ ግሽበት በዜጎች ላይ እያሳረፈ ያለው ጫና ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ ነው ።

ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ ሁለት የኢኮኖሚ ባለሙያዎች አሁን የኮሮና ቫይረስ ኢትዮጵያም ውስጥ ወረርሽኝ ሆኖ በመከሰቱ በአንጻሩ የገቢ እቃዎች መቀነስ በመታየቱ እንጂ የሚከሰተው የዋጋ ንረት ከዚህም ይብሳል ብለውናል።


 የይፋዊ እና የጥቁር ገበያ የምንዛሬ ተመን ዋጋን ማቀራረብም ብርን ከማዳከም የሚጠበቅ ውጤት ቢሆንም ይሄም አልተሳካም።በጥቁር ገበያ አንድ የአሜሪካ ዶላር በ45 ብር አካባቢ ነው እየተመነዘረ ያለው። ከመደበኛው ገበያ የዘጠኝ ብር ልዩነት አለው።ይህም የሆነው በመደበኛው ገበያ ብርን በማዳከም የሚጠበቀው የውጭ ምንዛሬ ግኝት ባለመሳካቱ ነው።


 መንግስትም አሁን ላይ መሰረታዊ የሚባሉ የምጣኔ ሀብቱን ችግሮች ከመፍታት ይልቅ የአለማቀፍ የገንዘብ ተቋማት ምክረ ሀሳብ የሆነው የብር ማዳከም ላይ አተኩሯልም ብለውናል የምጣኔ ሀብት ባለሙያዎቹ። ከሰሞኑ መንግስት ከአለማቀፉ የገንዘብ ተቋም :አይኤምኤፍ :ለሁለተኛውን ዙር ማለትም ከሁለት መቶ ሚሊየን ዶላር በላይ ገንዘብን ሊያገኝ ነው መባሉም የምንዛሬ ተመኑ አካሄድ ሊቀጥል እንደሆነ ዋዜማ ራዲዮ ከምንጮቿ ሰምታለች።


ኢትዮጵያ ከነ አይ ኤም ኤፍ ጋር በኢኮኖሚ ማሻሻያዎች ላይ ከስምምነት ደርሳ ፊርማዋን ስታኖር ; ቢሊየን ዶላሮችን በምላሹ ያገኘቸው የኢኮኖሚ ማሻሻያዎቹ የራሳቸው አሉታዊ ጎንን ስለሚያስከትሉ በምላሹ በሚገኘው ገንዘብ የምጣኔ ሀብት የማረጋጋት ስራዎችን እንድትሰራ ነው። ነገር ግን መንግስት የሚያገኘውን ገንዘብ የኢኮኖሚውን ትክክለኛ ችግር ለመፍታት ተጠቅሟል ማለት ይቸግራል። እነዚህ ጉዳዮች መንግስትን መንታ መንገድ ላይ ጥለውታል። በምንዛሬ ተመን ላይ መንግስት ለአለማቀፍ ተቋማት ቃል የገባውን ይተግብር እንጂ የመንግስት የልማት ድርጅቶችን ወደ ግል የማዘዋወሩ : የመንግስት ወጭን የመቀነሱና የግብር ገቢን የማሳደግ ጉዳይ ላይ በሚፈለገው መልኩ አልሰራም። ወጪን የመቀነሱና ግብርን መጨመር ያለመቻሉ ችግር ኮሮና ቫይረስ በኢኮኖሚው ላይ ያደረሰው ሊሆን ቢችልም የዶክተር አብይ መንግስት ወጭ እዳ እንዳለበት ሀገር እንዳልሆነና ቅድሚያ ለሚሰጣቸው ዘርፎች ቅድሚያ ያልሰጠ እንደሆነ የሚያሳይ ነው ሲሉ የምጣኔ ሀብት ባለሙያዎች ይተቻሉ።


 ከምንዛሬ ተመን ውጭ ያሉ የኢትዮጵያ መንግስት የኢኮኖሚ ማሻሻያ እንቅስቃሴ ያላስደሰታቸው እነ አይኤምኤፍና የአለም ባንክ በቢሊየን ዶላሮች ሊሰጡት ያሰቡትን  ብድር ያዝ በማድረግና ስምምነታችንን እናቋርጣለን በማለት ጭምር ጫና ሲፈጥሩ እንደነበር ዋዜማ ራዲዮ ከታማኝ ምንጮቿ ሰምታለች።


ሰኔ ወር ማለቂያ ላይ የኢትዮጵያ መንግስት ከአለም ባንክ ሊለቀቅለት የነበረው 500 ሚሊየን ዶላር እንዲዘገይ የመደረጉ ጉዳይ በወቅቱ መንግስት እንዳስተባበለው ገና ድርድሩ ሳያልቅ የሆነ አይደለም። ዋዜማ ራዲዮ ባደረገችው ማጣራት የአለም ባንክ በወቅቱ እንዲዘገይ ያደረገው 500 ሚሊየን ዶላር ሊሰጥ የመጨረሻ ደረጃ የደረሰ ነበር። በወቅቱም የኢትዮጵያ መንግስት ገንዘቡ የዘገየበትን ምክንያት አስመልክቶ ለአለም ባንክ ጥያቄ አቅርቦ እስካሁን ያላለቀ ውይይት እየተደረገበት እንደሆነም ሰምተናል። ይህን ጉዳይ ከታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ድርድር ጋር ያገናኙት ነበሩ። የዚህ መነሻ የአለም ባንኩ ፕሬዝዳንት ዴቪድ ማልፓስ 500 ሚሊየን ዶላሩ የተከለከለ ሰሞን በትዊተር ገጻቸው ስለ ህዳሴው ግድብ የሶስትዮሽ ድርድር እና የምንዛሬ ተመንን በገበያ የሚወሰንበትን መንገድ አስመልክቶ ከጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ጋር እንደተወያዩ የገለጹ ሰሞን የተሰማ መረጃ በመሆኑ ነው።


 መንግስት በብሄራዊ  ባንክ በኩል እተገብራቸዋለሁ የሚላቸው አሰራሮችም የሀገሪቱ ኢኮኖሚ አሁን ባለበት ሁኔታ በዚህ ቀን ሊተገበር ይችላል ተብሎ መገመት የማይቻል እና መንግስት ለአለማቀፍ የገንዘብ ተቋማት ቃል ስለገባ ብቻ የሚናገረው እንደሆነ ነው ያነጋገርናቸው የኢኮኖሚ ባለሙያዎች የገለጹልን። ለአብነት የብሄራዊ ባንኩ ገዥ ይናገር ደሴ ከሰሞኑ ኢትዮጵያ በገበያ የሚወሰን የውጭ ምንዛሬ ተመን ከሶስት አመት በሁዋላ ይኖራታል ብለዋል።


ኢትዮጵያ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያን በሶስት ዓመት ነው ለመተግበር ለአለማቀፍ አበዳሪዎች ቃል የገባችው። ከዚህ የሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ ትግበራ ላይ ደግሞ አንድ አመት ተጠናቆለታል። ስለዚህ አሁን በብሄራዊ ባንኩ ገዥ የተቀመጠው የጊዜ ገደብ አጠራጣሪ ነው። በሌላ በኩል አሁን ላይ በከፍተኛ ደረጃ ጨምሮ ለወራት ከሀያ በመቶ በታች አልወርድም ያለውን የዋጋ ግሽበት ወደ ነጠላ አሀዝ ለማውረድ እርግጠኝነት በሌለበት ሁኔታ እንዲህ አይነት አቅጣጫ ማስቀመጥ አዋጭ አይደለም። እንዲሁም የወለድ ምጣኔን ከዋጋ ግሽበት ጋር የማጣጣም ስራም ከሶስት አመት በሁዋላ ለመተግበር መታሰቡም ተሰምቷል። የወለድ ምጣኔ ጉዳይም ቀጥታ ከዋጋ ግሽበት ጋር የሚገናኝ ነው። ምክንያቱም አሁን ባለው የዋጋ ግሽበት ለባንክ ገንዘብ አስቀማጮች ወለድ ይታሰብ ከተባለ ሰዎች ገንዘብ ለመበደር የሚጠየቁት ወለድ ደግሞ አሁን ካለው የዋጋ ግሽበትም በላይ ይሆናል።ምክንያቱም ባንኮችም ትርፍ ፈላጊ በመሆናቸው። ይህ ደግሞ ለኢንቨስትመንት መበደርን ከባድ ያደርገዋል።


ያነጋገርናቸው የኢኮኖሚ ባለሙያዎች : መንግስት አሁን ላይ ለመተግበር የሚያወጣቸው እቅዶች በትክክልም የሀገሪቱ የኢኮኖሚ ችግር የሆኑትን ለመቅረፍ የሚያግዙ በተለይም የዋጋ ግሽበትን የመሳሰሉ ችግሮችን የሚያስቀሩ መሆን አለባቸው ብለውናል። ከአለም አቀፍ የገንዘብ አበዳሪ ተቋማት ጋር የተገቡ ስምምነቶችንም ቢሆኑ እንደ ኮቪድ 19 አይነት ወቅታዊ ችግሮችን ከግምት ውስጥ እንዲገቡ በማድረግ ማሻሻል ያስፈልጋል ይላሉ ባለሙያዎቹ። [ዋዜማ ራዲዮ]

To contact editors write- wazemaradio@gmail.com