Lema Megerssa head of Oromia region, Photo ENA
Lema Megerssa head of Oromia region, Photo ENA

 

ዋዜማ ራዲዮ- የኢህአዴግ አራቱ አጋር ፓርቲዎች ዛሬ ወይም ነገ ምሽት በብሔራዊው የቴሌቪዥን ጣቢያ ቀርበው መግለጫ በመስጠት ሕዝቡን ያረጋጋሉ ተበሎ ይጠበቃል፡፡

በህዝቡ ዘንድ ተስፋ ተደርጎ የነበረው ለውጥ ተቀልብሷል የሚል አስተያየት በስፋት እየተስተዋለ ሲሆን በተለይ አቶ ለማና ድርጅታቸው ወደው አልያም ተገደው የህዝቡ ፍላጎት እንዲዳፈን ተደርጓል የሚሉም ብዙዎች ናቸው።አቶ ለማ መገርሳን ጨምሮ የሕወሓትና የብአዴንና የደኢህዴን ሊቀ መንበሮች በሁለት ሳምንቱ የኢህአዴግ ሥራ አስፈጻሚ ጉባኤ መልክና ይዘት፣ በአገሪቱ መጻኢ እድሎችና በአዲስ የጋራ አመራር ስልቶች ዙርያ ሰፋ ያለ ማብራሪያ ይሰጣሉ፡፡
ከኦህዴድ ጽሕፈት ቤት አንድ የዋዜማ ምንጭ እንደተናገሩት ፓርቲዎቹ ወደ ማዕከላዊ ኮሚቴ ተመልሰው ግምገማ
ለመጀመር ዝግጅትእያደረጉ ነው፡፡ ከሐዋሳው የኢህአዴግ ጠቅላላ ጉባኤ በፊት በሚደረገው ግምገማው በሥራ
አስፈጻሚው የተደረሱባቸውን አንኳር አጀንዳዎች የአራቱ ፓርቲዎች አመራሮች ለከፍተኛ ካድሬዎች ያሰርጻሉ ብለዋል፡፡
በግምገማው ወቅትና ከግምገማው በኋላም የተወሰኑ ሚኒስትሮችም ከሥራ ይሰናበታሉ ብለዋል፡፡ ኾኖም ተሰናባች
ሚኒስትሮች እነማን እንደሆኑ ለጊዜው መረጃው እንደሌላቸው ለዋዜማ ተናግረዋል፡፡
በዛሬው ምሽት አልያም ነገ በሚሰጠው መግለጫ ላይ አቶ አባዱላ የሥራ መልቀቂያ ጥያቄያቸውን ለምን እንደቀለበሱ ለሕዝብ መግለጫ ይሰጣሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ይህ በእንዲህ እያለ ማንኛውም አመጽ ለመመከት መከላከያና ፌደሬራል ፖሊስ በተጠንቀቅ እንዲቆሙ ጠበቅ ያለ
መመሪያ ተላልፏል፡፡ በአዲስ አበባም ሆነ በክልል ዩኒቨርስቲዎች አካባቢም ቅኝት እንዲደረግ የጸጥታና ደህንነት
ካውንስል ዝግጅት አድርጓል ተብሏል፡፡ ከሰሞኑ የሚነሱ አመጾች ማስቆም ካልተቻለ በቀጣይ ወራት ከፍተኛ ዋጋ
ሊያስፍሉ ይችላሉ፣ ከቁጥጥር ውጭ ሊሆኑም ስለሚችሉ ጠንካራ ክትትልና የጸጥታ ቁጥጥር እንዲደረግ፣ ችግር
በሚፈጥሩት ላይም ጫን ያለ እርምጃ እንዲወሰድ ተወስናል ብለዋል የዋዜማ ምንጭ፡፡