ዋዜማ ራዲዮ- የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 1ኛ የፀረ ሽብር እና በህገ መንግስት ላይ የሚደርጉ ወንጀሎች ችሎት የእነ እስክንድር ነጋን መዝገብ ዛሬ ጥር 05 ቀን 2013 ዓም ረፋድ ላይ ተሰይሞ ተመልክቷል።

ተከሳሾቹ ወንጀሉን አልፈፀምንም በማለት የእምነት ክህደት ቃላቸውን መስጠታቸውን ተከትሎ ቸሎቱ አቃቤ ህግ ከመጋቢት 29 2013 ዓ.ም ጀምሮ ምስክሮቹን እንዲያሰማ ቀጠሮ መስጠቱ ይታወሳል።

ይሁን እንጂ እነ እስክንድር ነጋ በቀጣዩ ሀገር አቀፍ ምርጫ መሳተፍ ይችሉ ዘንድ የፍትህ ስርዓቱ እንዲፋጠን እና አጫጭር ቀጠሮ እንዲሰጥ ችሎቱን ሲጠይቁ ቆይተዋል።

ይህን ተከትሎም የተከማቹበትን መዝገቦች ከሌሎች ችሎቶች ጋር በመከፋፈል ያመቻቸው ችሎቱ ተከሳሾቹ ዛሬ በችሎት እንዲገኙ በማድረግ ምስክር መሰማት የሚጀመርበትን ቀን ወደ ጥር 26 ማቅረቡን ገልፆላቸዋል።

የዋዜማ ሪፖርተር እንደዘገበችው አቃቤ ህግ አሉኝ ያላቸውን 21 ምስክሮች በተስጠው ቀጠሮ በግልፅ ችሎት ማሰማት ይጀምራል።

ከዚህ ቀደም አቃቤ ህግ ምስክሮቹን በዝግ ችሎት እና ከመጋርጃ በስተጀርባ እንዲሰማለት ችሎቱን ቢጠይቅም ችሎቱ ውድቅ እንዳደረገበት ይታወሳል። [ዋዜማ ራዲዮ]