Debretsion G.Michael- Deputy head of Tigray region- FILE

ዋዜማ ራዲዮ- ከሀገሪቱ የተለያዩ ክልልሎች የተፈናቀሉ የትግራይ ክልል ተወላጆችን መልሶ ለማቋቋም በማሰብ የክልሉ መንግስት የተለያዩ እርምጃዎችን እየወሰደ ይገኛል፡፡ ከነዚህ መካከል ተፈናቃዮችን የቤት ባለቤት ለማድረግ የተጀመረው ጥረት አንዱ ነው፡፡

መቀሌን ጨምሮ በተለያዩ የክልሉ ከተሞች ውስጥ የቤት መስሪያ ቦታ ለመስጠትም ተፈናቃዮችን የመመዝገብ ስራም ተጀምራል፡፡ በተለይ በክልሉ በሚገኙ ታላላቅ በሆኑ 8ቱ ከተሞች ለነዚሁ ዜጎች የተዘጋጀው ቦታ 70 ካሬ ሜትር ሲሆን ሙቀት በሚበዛባቸው ቆላማ አካባቢዎች ደግሞ እስከ 140 ካሬ ሜትር ቦታ ለመስጠት ታስቦ ነው እንቅስቃስው የተጀመረው፡፡

ይህንን እድል ለመጠቀም የሚያመለክቱ ተፈናቃዮች ደግሞ በቁጥር 20 እየሆኑ መደራጀት የሚጠበቅባቸው ሲሆን እንደቅድመ መያዣ የሚሆን 20 ሺሕ ብርም እንዲያሲዙ ይጠበቃል፡፡ ዋዜማ ሬዲዮ ለጉዳዩ ቅርበት ካላቸው ምንጮች እንዳጣራችው ከሌላ ክልል ተፈናቅያለሁ ብሎ የሚያመለክት የክልሉ ተወላጅ በተባለው አካባቢ ስለመኖሩ እና መፈናቀሉን የሚያውቁ ሶስት የሰው ምስክር ይዞ በመቅረብ እንዲመዘገብ ማድረግ አልያም በሚኖርበት አከባቢ ነዋሪ መሆኑን የሚሳይ መታወቂያ ማቅረብም ሌላው አማራጭ የማረጋገጫ ስልት ነው፡፡


በክልሉ ይህንን ምዝገባ ከሚያከናውኑ ምንጮቻችን ለማጣራት እንደሞከርነው ሶስት የሰው ምስክር በማቅረብ ተፈናቃይ ነኝ የሚለውን ለማረጋገጥ የሚሞክሩ ሰዎች የሚያቀርቧቸው የሰው ምስክሮች በትውውቅ እና የቅርብ ዘመድን ጭምር በመጠቀም መሆኑ የምዝገባውን ሁኔታ አስቸጋሪ አድርጎታል፡፡


አሁን የሰው ምስክር በማቅረብ የሚደረገውን ምዝገባ ይበልጥ መታወቂያ ላይ እንዲያተኩር ቢፈለግም ይህም አማራጭ ችግር እንደፈጠረ ነው ምንጮቻችን የሚናገሩት፡፡ ከትግራይ ክልል ውጭ ነዋሪ የሆኑ የትግራይ ተወላጆች ተፈናቃይ ነኝ በማለት ከተለያዩ ክልሎች መታወቂያ በማውጣት ጭምር ለመመዝገብ እያመለከቱ ነው፡፡


ይህ ደግሞ በዋናነት የአዲስ አበባ ነዋሪ የሆኑ ሰዎች ጭምር መታወቂያውን በክፍያ ከሌሎች በተለይም ከአማራ እና ኦሮሚያ ክልሎች በማግኘት በተፈናቃይ ስም ለማመልከት ወደ ትግራይ እንደሚጓዙ ታውቋል፡፡ የዋዜማ ምንጮች እንደሚናገሩት ተፈናቃዮቹ 20 ሆኖ ተደራጅቶ የቤት መስሪያ ቦታ ለማግኘት በሚያደርጉት ጥረት ውስጥ በአዲስ አበባ አካባቢ በነዋሪነት የሚታወቅ ግለሰብ ከኦሮሚያ ክልል ተፈናቃይ ነኝ ብሎ መታወቂያ ይዞ ማመልከቱ ጭምር ጥቆማ እንደደረሳቸው ይናገራሉ፡፡


አሁን ደግሞ በምዝገባ ሂደቱ ከግለሰብ የምስክር ማስረጃዎች ይልቅ መታወቂያ ይዞ ለሚመጣ ተፈናቃይ ነኝ ለሚል አመልካች ቅድሚያ መሰጠቱ ሂደቱን ቀላል በማድረጉ ተፈናቃይ ያልሆኑ ሰዎች መታወቂያውን በተለያየ መንገድ እስካገኙ ድረስ ቀድመው መስተናገዳቸው አመልካቾቹ ተፈናቅልንባቸው የሚሏቸው የአማራ እና ኦሮሚያ ክልሎችን መረጃ ለመጠየቅ እና የመታወቂያዎቹን ትክክለኛነት ለማጥራት ደግሞ በክልሎቹ መካከል ያለው ግንኙነት ሂደቱን የማይሞከር እያደረገው ነው፡፡


የትግራይ ብሄራዊ ክልል በጥቅምት ወር ተፈናቃዮችን መልሶ ለማቋቋም በተዘጋጀው ገቢ ማሰባሰቢያ ወቅት የተፈናቃዮቹን ቁጥር 45ሺሕ አካባቢ እንደሆኑ ይግለጽ እንጂ አሁን ክልሉ ከሌሎች የሀገሪቱ ክፍሎች ተፈናቅለውብኛል ብሎ የመዘገባቸው ዜጎች ቁጥር እስከ 91 ሺህ መድረሱ ነው የሚነገረው፡፡ ባለፉት 6 ወራት ግን በተለየ ሁኔታ የክልሉ ተወላጆችን በዚህ ቁጥር ልክ ያፈናቀለ ልዩ ክስተት መኖሩ ግን አይታወቅም፡፡ [ዝርዝር የድምፅ ዘገባ ከታች ይመልከቱ ]

https://youtu.be/0hYdgM3tGdI