Wollega University-FILE
Wollega University-FILE

2009! መልካም የአመጽና የትምህርት ዘመን ይሁንላችሁ!

በዘመናዊ ኢትዮጵያ ታሪክ የመብት ጥያቄን ያማከለ የአመጽ ችቦ የሚለኮሰው በአመዛኙ ከትምህርት ተቋማት ኾኖ ቆይቷል፡፡ በቅርብ ጊዜ አገሪቱ ያስተናገደቻቸው አመጾችና ሕዝባዊ እምቢተኝነት ግን በዩኒቨርስቲ ተማሪዎች የተለኮሱ አልነበሩም፡፡ እንዲያውም ዩኒቨርስቲዎች ለእረፍት በራቸውን በዘጉበት ወራት ነው አገሪቱ ጠንከር ያሉ ግጭቶችን እዚያም እዚህም ስታስተናግድ የከረመችው፡፡ ወጣቶች ከሁሉም የኢትዮጵያ ክፍል ተውጣጥተው አንድ የትምህርት ካምፕ ዉስጥ ሲሰባሰቡ ምን ሊፈጠር ይችላል? ወይንሸት ሞላልኝ በ2009 የአመጹ ችቦ ከሕዝብ ወደ ተማሪ ቤት መግባቱ አይቀሬ ነው ትለናለች፡፡

መንግሥት በመስከረም መጨረሻ 33 አዳዲስ የጦር ግንባሮች ይከፈቱበታል፡፡ ይህ የተጋነነ ገለጻ ሊመስል ይችላል፡፡ አይደለም፡፡

የዩኒቨርስቲዎቻችንን ዓመታዊ ከራሞት፣ ዉሎና አዳር ለሚከታተል፣ የአገሪቱን ወቅታዊ የትኩሳት መጠን ለሚለካ፣ መጪውን ጊዜ አሻግሮ ለመተንበይ ለሚሞክር ሁሉ ዐረፍተ ነገሩ መሬት ጠብ የማይል የነብይ ቃል ኾኖ ይታየዋል፡፡

ያለፉትን ሦስት ዓመታት ብቻ ለናሙና ብንወስድ አገሪቷ ካሏት ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት በዘጠኙ ግጭቶች ተከስተዋል፡፡ ይህ ቁጥር ካሉን 33 ዩኒቨርስቲዎች ሲሶውን ይይዛል፡፡ የግጭቶቹ ምክንያት፣ ስፋትና ጥልቀት ቢለያይም ተቋማቱ ሰላም እንደራቃቸው አሀዙ ጮክ ብሎ ይናገራል፡፡ በሐረማያና ወለጋ በተደጋጋሚ፣ በአዳማ፣ ጅማ፣ ጎንደር፣ አርባምንጭ፣ ሐዋሳና ዲላ በመጠኑ፣ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ በከፊል ግጭቶች፣ (ተቃውሞዎች) ተከስተዋል፡፡

አለመታደል ኾኖ በዩኒቨርስቲዎቻችን የሚቆሰቆሱ ግጭቶች መነሾ እና ውጤታቸው የሚገናኙ ኾነው አይታዩም፡፡ የካፌ ሽሮ ቀጠነብን ዓይነት ቀጭን ምክንያት እንኳ ሄዶ ሄዶ የብሔር መልክን መያዙ አይቀርም፡፡ እስከዛሬ በየትኛውም አጋጣሚ የተጀመሩ ግጭቶች የብሔር መልክ ለመያዝ ጊዜ ሲወስድባቸው አይታይም፡፡ መቀሌ ዩኒቨርስቲ አዲ ሀቂ ካምፓስ በተሰናዳ ወርሃዊ የሥነጽሑፍ ምሽት አጼ ሚኒሊክ ተዘክረው አጼ ዮሐንስ ተዘለዋል የሚል ምክንያት ለፕሮግራሙ መቋረጥ ምክንያት ሆኗል፡፡ በአዳማ ዩኒቨርስቲ አንድ የትግራይ ተወላጅ ባልታወቁ የኦሮሞ ተወላጆችተገደለ የሚለው ወሬ በመላው የአገሪቱ ዩኒቨርስቲዎች ፍርሃት እንዲነግስ ማድረጉ ይታወሳል፡፡ በጊንጪ የአንድ ትምህርት ቤት መሬት ለባለሐብት ተላልፏል የሚለው ምክንያት የኦሮሚያን የማያባራ የተቃውሞ ሰደድ ወልዷል፡፡ በዲላ የአንድ ተማሪ በወጣበት መቅረት ሙሉ ግጭት እንዲቆሰቆስ ምክንያት ኾኗል ፡፡ በቦንብ ፍንዳታ አንድ ተማሪ ሞቷል፡፡ ሟች ሰው መሆኑ ብቻውን ሐዘን ለመቀመጥ በቂ አይሆንም፡፡ ደሙ ይተነተናል፡፡ዘሩ ይመነዘራል፡፡ ለሐዘን የሚቀመጡትም የርሱ ዘር አባላት ብቻ ይሆናሉ፡፡ ይህ በከፊል መንግሥት ከሚከተለው የብሔር ፖለቲካ የሚመነጭ ነው፡፡ በሩብ ምዕተ ዓመት የተገኘ የኢህአዴግ ፍሬ ነው፡፡

ብዙዎቹ ተማሪዎች ከመጀመርያ ዓመት ጀምሮ በግቢ ዉስጥ ከኢትዮጵያዊነት ይልቅ በብሔር ላይ እንዲያተኩሩ የሚያስገድዷቸው ሁኔታዎች መኖራቸው ሌላው ምክንያት ነው፡፡

ፍሬሽማን እያለን ገና ዶርም በመጀመርያ አዳራችን እዚህ ዶርም ኦሮሞ የሆናችሁ ይቺን ፎርም ሙሏት ተባልን ትላለች ለዚህ ጽሑፍ ዝግጅት የዋዜማ ዘጋቢ ያነጋገረቻት ወጣት፡፡ ድሮ አገርህን እወቅ የሚሉ የቱሪዝም ክበባት አሁን ብሔርህን እወቅ ወደሚል ወርደዋል፡፡ የብሔር ማንነትን ጥያቄ የሚያቀርቡት ደግሞ ሲኒየር ተማሪዎች እንጂ የአስተዳደር ሰዎች አልነበሩም፡፡ ከአዲስ አበባ የመጣን ልጆች በሁኔታው ሁላችንም ተደናገጥን፣ የተወሰኑት ግን ፎርሙን ተቀብለው ሞሉ ትላለች ያን ማለዳ እንደ ክፉ አጋጣሚ የምታስታውሰው ወጣት፡፡

ነባር ተማሪዎች አዳዲስ ተማሪዎችን የሚቀበሉት በብሔርና በኃይማኖት ተደራጅተው ነው፡፡ ጥናት የሚካሄደው በብሔር ነው፡፡ ይህ አሰላለፍ ተማሪዎቹ እስኪመረቁ የሚቀጥል ሲሆን ብሔር ነክ ግጭቶች ከተነሱም መቧደኑ ራስን ከአላስፈላጊ ጥቃት ለመከላከል ይረዳል ይላሉ ተማሪዎች፡፡ የጥናት ቡድኖች ሲዋቀሩም ተማሪዎች ፈጥነው ወደሚመስላቸው ብሔር ይሳባሉ፡፡ ፈተና ነክ ጉዳዮች ሲያወሩ ብዙ ተማሪዎች አማርኛን ትተው በየራሳቸው ቋንቋ ማንሾኳሾክ ይመርጣሉ፡፡ ይህ በሌላው አብሮ ነዋሪ የመገለል ስሜትን ከመፍጠሩም በላይ እርሱን የሚመስሉትን አነፍንፎ የመፈለግ ግዴታ ዉስጥ ይከተዋል፡፡

ትንሿ ኢትዮጵያ

የትምህርት ሚኒስትሩ አቶ ሽፈራው ሽጉጤ መስሪያ ቤታቸው በሚቀጥረሉት ቀናት በተዋረድ 28 ሚሊዮን ወላጆችን እንደሚያወያይ ገልጸዋል፡፡ ይህ እንግዳ ነገር እንዲሁ የመጣ ዱብዕዳ አይደለም፡፡ ከሚሊዮን የሚልቁ ተማሪዎች ወደ ትምህርት ገበታቸው ሲሄዱ ግጭት እንዳይቀሰቀስ ከፍተኛ ስጋት በመንግሥት የጸጥታ ካቢኔ ላይ ጭምር በመኖሩ ነው፡፡ ወላጆችን ብዙ ምክርና ትንሽ አብዮታዊ ዲሞክሲን ማጋት የግዛት ዘመንን ለማርዘም እንደምርጫ ታይቶ ነው፡፡ የሚያመጣው ለውጥ ባይኖርም፡፡

የመስቀል በዓልን ተከትሎ 33 ዩኒቨርስቲዎች በራቸውን ይከፍታሉ፡፡ ትንሽዋን ኢትዮጵያ በዩኒቨርስቲ ትወከላለች፡፡ 33 ትንንሽ ኢትዮጵያዎች በአንድ ጀንበር ተፈጠሩ እንደማለት ነው፡፡ ለግማሽ ሚሊዮን ብዙም ያልጎደሉ ወጣት ተማሪዎች ናቸው ወደነዚህ ዩኒቨርስቲዎች መትመም የሚጀምሩት፡፡ የነዚህ ተማሪዎች የብሔር ስብጥር ከወቅታዊው ፖለቲካዊ ጡዘት ጋር ሲዳበል መዓት ይዞ መምጣቱ የማይቀር ይመስላል፡፡ የመንግሥትን የቤት ሥራ ያበዛውም ይኸው ሀቅ ነው፡፡

በሰሞኑ ጋዜጣዊ መግለጫ ወላጆች ልጆቻቸውን ለመላክ ሰግተዋል የሚል ጥያቄ ከጋዜጠኞች የቀረበላቸው አቶ ሽፈራው ፍርሃቱ መሠረተ ቢስ እንደሆነ አድርገው ለማቅረብ ሞክረዋል፡፡ ማኅበራዊ ሚዲያው ፍርሃት እንዲፈጠር ፍላጎት አለው፣ ለምሳሌ አምና ኦሮሚያ ክልል የተለያዩ ቦታዎች ላይ ግጭቶች ተከስተዋል፣፣ ነገር ግን አንድም ተማሪ በብሔር ማንነቱ ምክንያት ጉዳት አልደረሰበትም፡፡ የሚያስፈራ ነገርም አልተከሰተም ሲሉ የአምናውን የኦሮሚያ ግጭት ሰላማዊነት ሊሰብኩ ሞክረዋል፡፡ በአመጽ ዉስጥ ሰላማዊነት ቦታ እንዳይኖራት የመንግሥት የጸጥታ ኃይሎች ባህሪ የሚፈቅድ አይሆንም፡፡

የትምህርት ሚኒስትሩ ምላሽ መሬት ላይ ያለውን እውነት የሚቀይር አይመስልም፡፡ ሥር የሰደደ ዘረኝነትና መቧደን በአንድ ድስት በሚቁላላባቸው ዩኒቨርስቲዎች እንዴትም አይነት ቁጥጥር ቢደረግ የብሔር ግጭትን ማስቀረት ይቻላል? ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት እንኳንስ አሁን፣ በደጉ ጊዜም የዘር ንክሻ ርቋቸው መቼ ያውቅና?

የትምህርት ሚኒስትሩ ከሰሞኑ ስጋት ከጋረደው ፈገግታ ጋር በሰጡት መግለጫ ነገሩ የሚያሳስብ አለመሆኑን ቢያስገነዝቡም ለወላጆች ያስተላለፉት መልዕክትና ተማሪዎች ወደተቋማቱ የተመደቡበት አሰራር የመንግሥትን የዉስጥ ፍርሃት አጉልቶ ያንጸባረቀ ነበር፡፡

ወላጆችን የምመክረውበዚች አገር ስም የማይምል የማይገዘት የለም፣ እቺን አገር እወዳታለሁ ብሎ ደረት መደለቅ በቂ አይደለም፣ በተግባር ይቺን አገር አንድነቷን መጠበቅ ያስፈልጋል፡፡ ሲሉ ካስገነዘቡ በኋላ አንዱ ብሔር ብሔረሰብ ለሌላው ብሔር ብሔረሰብ ኃላፊነትን ይወስዳል ሲሉ የአካባቢው ነዋሪ ተጠያቂ መሆኑ እንደማይቀር ጠቁመዋል፡፡ ምክራቸውን ያሳረጉትም ለብሔር ብሔረሰቦች የወል አደራ በመስጠት ነበር፡፡ ይህ መልዕክት ሲጨመቅ የሚሰጠው ትርጉም ችግር መፈጠሩ አይቀርም፣ እኛም በፍርሃት እየራድን ነው፤ ኾኖም ዩኒቨርስቲ የሚገኝበት የእያንዳንዱ ክልል ሕዝብ ሰላሙ እንዳይደፈርስ ዘብ ይቁምልን፣ ሌላ ምን ማድረግ እንችላለን? የሚል ሆኖ እናገኘዋለን፡፡

ተማሪና ወላጅና ያስተሳሰረ አመጽ

በቅርብ የተነሱ አመጾች ልዩ መገለጫ እናቶች ለሰልፈኞች ዉኃ ያጠጡበት፣ ገበሬዎች ነፍጥ ያነሱበት፣ የኃይማኖት አባቶች የባረኩት መሆኑ ነው፡፡ ወላጅና ልጆች ለአመጽ እንዲህ ተሳስረው የሚያዉቁበት አጋጣሚ በኢትየጵያ ታሪክ እምብዛም አይገኝም፡፡

ዩኒቨርስቲው የሚገኝበት አካባቢ ሕዝብ ኃላፊነት ይወስዳል የሚለው የሚኒስትሩ ተማጽኖ አሁን መሬት ላይ ካለው ነባራዊ ሁኔታ ጋር የማይሄደውም ለዚሁ ነው፡፡ ብሔር ብሔረሰቦች ለሰላም ዘብ ይቁሙ የሚለው የሚኒስትሩ ተማጽኖ የፖለቲካ ትኩሳት ባጋለው ሚዛን ላይ ስናስቀምጠው ብዙም ኪሎ አያነሳም፡፡

ለምን ከተባለተማሪዎች የወላጆቻቸው ፍትህ ማጣት አንገብግቧቸዋል፣ አካባቢያቸው ከልማት መገለሉ አሟቸዋል፣ መንግሥት ለሕዝብ ያለው ንቀት አቁስሏቸዋል፡፡ መጀመሪያኑ የፍትህ፣ የእኩልነትና የልማት ጥያቄዎቻቸው የመነጩት ይመክሯቸዋል ተብለው ከሚጠበቁ ወላጆቻቸው እንደሆነም ጠንቅቀው ያውቃሉ፡፡ ሁኔታው መካሪና ተመካሪ የሚፈልግ አይመስልም፡፡ የዕድሜ ልዩነትን ያልገደበው የሕዝብ ጥያቄ ተነስቷል፡፡ ተማሪዎቹ ወደፊት በየተቋሞቻቸው የሚያነሷቸው የዲሞክራሲ ጥያቄዎች ከየትም የፈለቁ ሳይሆኑ ከወላጆቻቸው የመጡ ናቸው፡፡ ይህ ነው የኢህአዴግን መጪ ፈተና የሚያብሰው፡፡

የከተሜ ወላጆች ጭንቀት

መጪው ጊዜ ብሩህ እንደማይሆን የተረዱ ወላጆች ልጆቻቸውን ወደ ክልል ዩኒቨርስቲዎች ላለመላክ ማንገራገር ከጀመሩ ሰነባብተዋል፡፡ በተለይም በአምቦ፣ ሐረማያ፣ ጎንደርና ባሕርዳር ተማሪ የነበሩ የትግራይ ተወላጆች ክልላቸው ወደሚገኙ ዩኒቨርስቲዎች ዝውውር ለማድረግ መሯሯጥ የጀመሩት በመተማና ጎንደር የዘር ጥቃት ተጀመረ በተባለ ማግስት ነው፡፡ በትግራይ የሚገኙ 3 ዩኒቨርስቲ ፕሬዝዳንቶችም የተማሪዎቹን የአዛውሩን ጥያቄ የሚደግፉ ደብዳቤዎችን ሲለዋወጡ እንደከረሙ የዋዜማ ምንጮች ያስረዳሉ፡፡

የትምህርት ሚኒስትሩ በአንጻሩ ዝውውር የሚጠይቁትን ተማሪዎች፣ በተለይም ደግሞ ልጆቻቸውን ወደ ተቋማቱ ላለመላክ የሚያንገራግሩትን ኢትዮጵያን ለመበታተን የሚሰሩ ሲሉ በጅምላ ይከሷቸዋል፡፡

አንድን ተማሪ ወደሌላ ክልል አትሂድ የሚለው አባባል ይቺን አገር እንበትን እንደማለት ነው፡፡ ሲሉ ነበር አቶ ሽፈራው በቅርቡ በመሥሪያ ቤታቸው በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ የደመደሙት፡፡

የድርጅት አባል የመሆን ፈተና

አራቱ የኢህአዴግ ፓርቲዎች በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ዉስጥ እጃቸው ረዥም ነው፡፡ ተማሪዎችን መመልመል የሚጀምሩት ገና ከማለዳው ነው፡፡ የድርጅት አባል የሆነ ተማሪ የሥራ ዋስትና እንደሚሰጠው በአመራሮች ደረጃ ቃል ይገባለታል፡፡ ለምሳሌ ከዓመታት በፊትም ቢሆን ረብሻ በማያጣው ሐረማያ ዩኒቨርስቲ ተገኝተው ተማሪዎችን ለመመልመል የሞከሩት የያኔው ሚኒስትር ጁነዲን ሳዶና አቶ አባዱላ ገመዳ በዩኒቨርስቲው አዳራሽ ለሰበሰቧቸው የኦሮሞ ተማሪዎች የሚከተለው ተናግረው እንደነበር የዚህ ጽሑፍ አሰናጅ ታስታውሳለች፡፡ ሥራ ማግኘት በፍጹም ጥያቄ ሊሆንባችሁ አይገባም፣ እኛ እንኳን እናንተ በዲግሪ የተማራችሁትን ይቅርና ፊደል ያልቆጠሩትን አይደለም እንዴ ወረዳ አስተዳዳሪ የምናደርገው? በወቅቱ ሁለቱ ሹማምንት ደማቅ የድጋፍ ጭብጨባን ማግኘት ችለው ነበር፡፡ ቃላቸውን አላጠፉም፡፡ ብዙዎቹን የዚያን ዘመን የኦህዴድ ምሩቃን ወረዳዎችን እንዲያስተዳድሩ ሸንሽነው ሰጥተዋቸዋል፡፡ አንዳንዶቹ አሁን ከፍ ወዳለ ሥልጣን ተሸጋግረዋል፡፡

ዛሬስ?

ዛሬ አባልነት ዋጋው ዝቅ ብሏል፡፡ በርግጥ የድርጅት ከፍተኛ አባልና አመራር የሆኑ ተማሪዎች አመጽ ሊያቀጣጥሉ ይችላሉ ያሚሏቸውን ተማሪዎች ጠቁሞ በማስያዝ ብዙ ይተጋሉ፡፡ በአለቆቻቸው ዘንድ ሞገስን ለማግኘት ከህሊናቸው ጋር እየተጣሉም ቢሆን በርትተው ይሠራሉ፡፡ በሥርዓቱ ላይ የሰላ ትችት የሚሰነዝሩ መምህራንን ያስፈራራሉ፡፡ ለዚህ አገልግሎታቸው ፓርቲና መንግሥት የተቻለውን ዉለታ ይከፍላቸዋል፡፡ ከነዚህ ላቅ ያሉት በጉምሩክና ገቢዎች፣ በአየር መንገድ፣ በኢሚግሬሽን ሥራ ከየትም ተፈልጎ ይሰጣቸዋል፡፡ በተማሪነታቸው ንቁ ተሳትፎ የነበራቸው የድርጅት አባልነት ካርዳቸውን በአግባቡ የተጠቀሙ የተማሪ አመራሮች ከትምህርት ፍጻሜ በኋላ አካዳሚያዊ ዉጤታቸው ምንም ይሁን ምን በዩኒቨርስቲ አስተማሪነት የተቀጠሩበት አጋጣሚም ጥቂት አይደለም፡፡

አሁን ሁኔታዎች መልካቸውን እየቀየሩ መጥተዋል፡፡ ካለፉት 10 ዓመታት ወዲህ በሚሊዮን የሚቆጠር አባል ሲያግበሰብስ የኖረው ኢህአዴግ የኢሰፓ እጣ እየገጠመው ይመስላል፡፡ አባል ስለሆኑ ብቻ በሥራ የመንበሽበሽ ጉዳይ ፈተና ገጥሞታል፡፡ በተማሪ ኅብረት አመራርነት የቆዩና በስለላ የተሰማሩ ካልሆኑ በስተቀር አሁን ለድርጅት አባል ሁሉ ሥራ መሸለም የኢህአዴግ ጫንቃ የሚችለው ጉዳይ አልሆነም፡፡ አንዱ ምክንያት ብዙ መቶ ሺ ተማሪዎች አባል እየሆኑ በመምጣታቸው የተፈጠረ ችግር ነው፡፡ ይህ ሁኔታ አባል በሆኑና ባልሆኑ ተማሪዎች መካከል ልዩነቱ የቀጠነ እንዲሆን አስችሎታል፡፡ በዩኒቨርስቲ ቆይታቸው የድርጅት አባል ሆነው በሥራ ማጣት የሚንገላቱ ተማሪዎችም ቁጥር አሁን አሁን ቀላል አልሆነም፡፡ ከየአካባቢው ከሚነሱ የአመጽ ተካፋዮች የሚበዙቱ የድርጅት ካርድ በኋላ ኪሳቸው የያዙ ናቸው፡፡

ተማሪዎችን በገፍ የድርጅት አባል በማድረግ አመጽን ለመቆጣጠር አዳጋች የሆነውም ለዚሁ ነው፡፡

ብዝኃነት ግጭት ይወልዳል?

የፖለቲካ መሪዎች ዘውጋዊ ብዝኃነታቸው አገር ለመገንባት እንቅፋት እንደሆነባቸው ይናገራሉ፡፡ ብዝኃነት በራሱ ለቁርሾ መነሻ ሊሆን አይችልም ይላሉ በዘር ግጭቶች ዙርያ ጥናት ያደረጉ አያሌ ምሁራን፡፡ ኾኖም ነጻነትን በመቸር ካልታከመ ለአመጽ የተመቻቸ ሜዳን ይፈጥራል፡፡ ብዝኃነት ዉስጥ የሚከተሉት ነጥቦች ሲጓደሉ የአመጽና የግጭት በር መክፈታቸው አይቀርም፡፡

በብሔሮች መካከል የሚታይም ሆነ የማይታይ ሥነ ልቡናዊ የበታችነትና የበላይነት ሲኖር፣

የመጨቆን ስሜት ዉስጥ ዉስጡን የሚብላላ ሲሆንና ጭቆናን ለመተንፈስ መድረክ ሲታጣ፣

በወደፊት ዉስጥ የሚታይ የተስፋ ፍንጣቂ ሳይኖር ሲቀር፡፡ ለምሳሌ የቀደምት ተማሪዎች ተመርቆ ሥራ ማጣት በነባር ተማሪዎች ላይ ተስፋን ሊያሳጣ ይችላል፡፡ ባለፉት ሥርዓቶች በአንዳች የታሪክ አጋጣሚ ተጨቁነን ኖረናል የሚሉ ተማሪዎች በአንድ ላይ ሲኖሩና ሕመሙን የሚጋሩበት አጋጣሚ ሲፈጠር፣ ለየትኛውም አይነት ፖለቲካዊ ለፍልሚያ የመዘጋጀት ስሜትን ይፈጥራል፡፡ በአገሪቱ ያለው የመብት፣ የሥልጣንና የሀብት ክፍፍል አድሏዊ መሆን ዉስጥ ዉስጡን የሚያማቸው አእምሮዎች ሲሰባሰቡም ላቅ ያለ አመጽን የመቀስቀስ ጉልበት ያገኛሉ፡፡

የሁሉም በክልሉ ትርክት

ተማሪዎችን በየክልላቸው በሚገኙ ዩኒቨርስቲዎች ብቻ በማስተማር የብሔር ግጭቶችን ማስቀረት የሚለው ዘዴ ከ6 አመታት በፊት ተሞክሮ ብዙም ዉጤት አላስገኘም፡፡ አንዱ ፈተና የተማሪዎች ቁጥርና ክልሎች ያሏቸው ዩኒቨርስቲዎች ብዛት አለመመጣጠን ነው፡፡ ሌላው ፈተና ሁሉም የትምህርት ፕሮግራሞች በሁሉም ዩኒቨርስቲዎችና በሁሉም ክልሎች በተመጣጠነ መልኩ አለመገኘታቸው ነው፡፡

የጨነቀው እርጉዝ ያገባል እንዲሉ ዘንድሮ ግጭቶችን ለመቀነስ ሲባል ይህ ዘዴ በተቻለ መጠን ተግባራዊ እንዲሆን ተሞክሯል፡፡ ከአዲስ ገቢ ተማሪዎች ከ60 በመቶ የሚልቁት በሚገኙበት ክልል እንዲማሩ ለማድረግ ተሞክሯል፡፡

የትምህርት ሚኒስትሩ አቶ ሽፈራው ግን ይህን በከፊል አስተባብለዋል፡፡

ሁሉም ተፈታኞች በ33 ዩኒቨርስቲ የመመደብ እድል አላቸው፡፡ 40 በመቶ የሚሆኑትን ተማሪዎች በክልላቸው እንዲመደቡ ሞክረናል፡፡ ይህ ላለፉት ዓመታትም ስንከተለው የነበረው አሰራር ነው፡፡ አዲስ ነገር አይደለም፡፡ በዚህ ዓመትም በጥብቅ የምንከተለው አሰራር ነው፡፡ ካሉ በኋላ ይህን ማድረግ ለምን እንዳስፈለገ ተጠይቀው ሲመልሱ ግን ዋናው አላማ አገሩን የሚያውቅ፣ የአገሩን ባህል ታሪክ አኗኗር የሕዝቦች ሁኔታ የሚያውቅ ወጣት ለመፍጠር ነው፡፡ የሚል ድፍን ያለ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ እውነታው ግን ከዚህ የዘለለ ነው፡፡ ብዙ ተማሪዎች ከክልላቸው እንዳይርቁ እየተሞከረ ያለው ብሔር ነክ ግጭቶችን በተቻለ መጠን ለመቀነስ ታስቦ ነው፡፡ ከዩኒቨርስቲ ቅጥር ግቢ የሚነሱ የብሔር እሳቶች አካባቢን ብሎም አገሪቱን የማቃጠል እድል እንዳለው ከመረዳትም ጭምር ነው፡፡

2009 የአመጽ ዘመን ወይስ የትምህርት?

ዩኒቨርስቲዎች የትምህርት ገበታ ከመሆናቸው ባሻገር የአገሪቱ የፖለቲካ ትኩሳት መለኪያም ናቸው፡፡ በዘመናዊው የኢትዮጵያ ታሪክ የፖለቲካና አስተዳደር ጥያቄዎች መነሻ በአንድም ሆነ በሌላ መንገድ ከዩኒቨርስቲዎች ቅጥር ግቢ መሆኑም ይህንኑ የሚያጠናክር ነው፡፡

በየአቅጣጫው በሰላም መደፍረስ ናላው እየዞረ ያለው መንግሥት ከመስከረም መጨረሻ ጀምሮ የሚያሰማራቸውን ግማሽ ሚሊዮን የሚጠጉ ተማሪዎችን በምን ስልት የተቃውሞ ተሰላፊዎች እንዳይሆኑ ማድረግ ይችላል የሚለው የሚሊዮን ብር ጥያቄ ነው፡፡ በቅርብ ጊዜ ኦሮሚያ ላይ እንደታየው በከፍተኛ የትምህርት ተቋማትና በ2ኛ ደረጃ ተማሪዎች የአመጽ ቅብብሎሽ የሚቀጥል ከሆነ የስጋት መጡንን እጥፍ ያደርገዋል፡፡ መንግሥት 2009 ሰላማዊ የትምህርት ዘመን እንዲሆን የሚያስችል ቁመና ላይ ነው? ምን ማድረግስ ይችላል? ብዙዎች የሚጠይቁት ጥያቄ ነው፡፡

በተወሰኑ ዩኒቨርስቲዎች የተማሪ ፖሊሶችን በማሰማራት ሰላም ለማስጠበቅ ተሞክሯል፡፡ በተወሰኑ ዩኒቨርስቲዎች የተማሪ ማረፊያ ቤቶችን (እስር ቤቶችን) በማዘጋጀት ጭምር አመጽን ለማዳፈን ተሰርቷል፡፡ በአንዳንድ አካባቢዎች ለተማሪ ኅብረት አመራሮች የተጋነነ መብት በመስጠት (ሥልጣናቸው አስተማሪን እስከማባረር የሚደርስ ነው) በማስታቀፍ ተማሪን በእጅ አዙር ለማባበል ተሞክሯል፡፡ ግጭት በሚከፋባቸው እንደ ሐረማያና ጅማ ያሉ ዩኒቨርስቲዎች ደግሞ የጦር ሠራዊት ካምፕ ግቢ ዉስጥና በአቅራቢያው በማዘጋጀት ሠላምና መረጋጋትን ድንበር በሚጠብቅ ጦር ለማምጣት ተችሏል፡፡ ዘላቂ ባይሆንም፡፡

በአንጻሩ 2009 የትምርት ዘመን የአመጽ ዘመን ለመሆን የሚያበቁ አያሌ ምክንያቶችን መዘርዘር ይቻላል፡፡ አንዱና ዋንኛው ጉዳይ ተራግቦ የተቀጣጠለ አመጽ፣ ተቦክቶ የተጋገረ ቁጣ ከክረምት ወደ በጋ መሸጋገሩ ነው፡፡ የተማሪዎች ሁነኛ የመረጃ ምንጭ ማኅበራዊ ሚዲያዎቸ መሆናቸው ደግሞ የአመጽን ቀጣይነት የሚያረጋግጥ አጋጣሚ ነው፡፡ ይህም በትውልድ አካባቢያቸው የሚፈጠሩ ማናቸውን በደሎች ለመስማት ቅርብ ያደርጋቸዋል፡፡ ለዚህ ምላሽ የሚሰጡት ደግሞ በዩኒቨርስቲዎቻቸው ዉስጥ በማመጽ ሊሆን ይችላል፡፡

ለተማሪ ቧልት የታለሙ የዘረኝነት ቅንጣት ያለባቸው የሽንት ቤት ጽሑፍች ለተዋጣለት ረብሻና ሙሉ አመጽ በቂ ምክንያት በሚሆኑበት የከፍተኛ ተቋማት ግቢ የጥላቻ ንግግር እንደልብ የሚነዛባቸው ማኅበራዊ ሚዲያዎች በበዙበት ሁኔታ ሊፈጥሩት የሚችለው እሳት ቶሎ የሚጠፋ አይሆንም፡፡

ተማሪዎች ከትውልድ አካባቢያቸው ይዘዋቸው የሚመጧቸው የበደልና የመገፋት ታሪኮች ቂም በሆዳቸው አዝለው ለትምህርት እንዲታደሙ ያደርጋቸዋል፡፡ በማንኛውም አጋጣሚ የሚፈጠሩ መናኛ ግጭቶች ሙሉ የአመጽ ክተትን ሊያሳዉጁ የሚቻላቸውም ለዚሁ ነው፡፡

በተማሪዎች የሚነሱ አስተዳደራዊ ጥያቄዎች የቱንም ያህል ለመፍታት ፍቃደኛ ቢኮን ማሟላት የሚቻል አይሆንም፡፡ የተማሪ የቁስና የምግብ ጥያቄ አንድ ጊዜ ከተጀመረ ወደ መብት ጥያቄ ማደጉም ተፈጥሯዊ ነው፡፡

ብዙ ሺ ወላጆች በ2009 ልጆቻቸውን ከትምህርት ገበታ ለማቀብ ቆርጠው ተነስተዋል፡፡ ቤተሰብ ልጁን አርቆ ወደየትኛውም የዓለም ጫፍ ለትምህርት ቢልክ የማይሰማው ስጋት በአገሩ እንዲሰማው ሆኗል፡፡ ይህም ባለፉት 25 ዓመታት የተዘራው የሚታጨድበት ጊዜ ላይ መድረሳችንን ይነግረናል፡፡