Abysinia Plaza (ዋዜማ ራዲዮ)

ጤና ይስጥልኝ ጌታዬ!

ገረመው እባላለሁ፡፡ እሳት የላስኩ የፊንፊኔ ደላላ ነኝ፡፡ ምስጉን ጉዳይ ገዳይ ስለመሆኔ እግዜርም ሰይጣንም ያውቃሉ፡፡ ኪራይ ሰብሳቢ መሆኔን ድሪባም ኩማም ያውቃሉ፡፡

ዉሎ-አዳሬ ብሔራዊ፣ አመሻሼ “አብዮታዊ”፣ ላየን ባር ቤቴ፣ ቴሌ ባር ግዛቴ…

ጥሎብኝ አልረጋም፡፡ ካዛንቺስ ነው ሲሉኝ ሳሪስ፣ ቀበና ነው ሲሉኝ ባምቢስ!! ድሮስ ደላላ ምን ቀልብ አለው ብለው ነው!

እርስዎ ግን እንዴት ከርመዋል?

ግንቦት 5 ቁርጡን የሚያውቀው ወዳጄ የጠቅል አመልጋ ልጅ አንድ መቼም መስማት የማይወደው ማስታወቂያ አለ፡፡ ‹‹…ምክንያቱም ያልተገነባ አንሸጥማ!!›› የሚል፡፡ ያ የሼኩ ነገረ-ፈጂ የአበበ ባልቻ ሬዲዮ ነው ደጋግሞ እንዲያ የሚለው፡፡

ያልተገነባ የማይሸጠው ማነው አይሉም ታዲያ? ኖሆች ናቸው፡፡ ሦስቱ የማይሰምጥ መርከብ ላይ የተቀመጡ ልጆች አሉ፡፡ እኔ የጋሽ ዘሪሁን ፈልፈላዎች እያልኩ እጠራቸዋለሁ፡፡ ጎበዝአየሁ፣ ዳዊትና ቴዎድሮስ ይባላሉ፡፡

ጌታዬ! ይሄኔ እኮ ጋሽ ዘሪሁንን አያውቋቸው ይሆናል፡፡

ጋሽ ዘሪሁንማ የ22 አድባር ማለት ናቸው፡፡ እንኳን እርስዎ ወያላ ያውቃቸው የለም እንዴ? አገር በገንዘብ ያቀኑ ጀግና ሽማግሌ፡፡ ድሮ በኛ ጊዜ 22-አካባቢ ለአመል አንዲት ፎቅ እንኳ አልነበረችም፡፡ ከዘሪሁን ሕንጻ በቀር፡፡ እርግጥ ነው ወረድ ብሎ ፕላዛ ነበር፤ እርግጥ ነው ማዶ ላይ አክሱም ሆቴል ነበር፡፡

ያኔ ፎቅ…. እንኳን ለግለሰብ ለመንግሥትም ብርቅ ነበራ፡፡ 

አሁንማ ወይዛዝርት ሁሉ  “መኪና አለው?” ማለት ትተው “ፎቅ አለው?” ነው የሚሉት አሉ፡፡ ክፉ ጊዜ!

እንኳን ሰው ፎቅ የረከሰበት ዘመን፡፡

እነ ጎላጎል ብሩን ከየት ጎልጉለው ፎቅ ባንድ ጀንበር ማቆም እንደጀመሩ እንጃ እንጂ  እንደነገርክዎ ድሮ ቀላል አልነበረም፡፡

ብቻ ጌታዬ! ጋሽ ዘሪሁን ለኔ የረዥም ዘመን ደንበኛ ብቻ ሳይሆን ጀግና ሽማግሌ ናቸው፡፡ ጥረው ግረው ለትውልድ የሚቆይ ቅርስ ያቆሙ የልማት ታጋይ፡፡ በብርታታቸው ዘሪሁን የእድር ስም ሳይሆን የሰፈር ስም ለመሆን በቃ፡፡ በሺ የሚቆጠር ወያላ ሳይወድ በግድ ስማቸውን በቀን ሺ ጊዜ ይጠራዋል፡፡

ጋሽ ዘሪሁን በሕይወት አለ፡፡ ያቺን ሮዝማኑን እያጨሰ፡፡ ያቺን እህል የቀመሰ የማትመስል ደቃቃ ሰውነቱን ይዞ አለ፡፡  ያቺኑ ጥልፍልፍ ጫማ በጣሊያን ሱፍ ገድግዶ፣ አማርኛና ኦሮምኛውን እያቀላጠፈ አሁንማ አለ፡፡ 80 አያልፈውም ብላችሁ ነው!? መነጽር እንኳ አያጠልቅም እኮ፡፡ የእጅ ሰዓት እንኳ አያስርም እኮ፡፡ ምነው ስለው “ሰዓት ለማሰር የማጠፋው ሰዓት የለኝም” ይለኝ ነበር፡፡ አይ ጋሽ ዘሪሁን!

አሁን በርካታ ጊዜውን የሚያሳልፈው ኮተቤ አካባቢ በስተርጅና እድሜው ባስገነባው ሰማይ ጠቀስ ፎቅ ዉስጥ ነው፡፡ በሳምንት አንዴ በልጆቹ ታጅቦ ባለቤቱን አስከትሎ ወደ 22 ይመጣል፡፡ ወደራሱ ዘሪሁን ሕንጻ፡፡

ጋሽ ዘሪሁንን ሳውቀው ቤተክርስቲያን ሳሚ ነበር፡፡ ባለቤቱም እንዲያ ናቸው፡፡ የተቀናጀ ጸሎታቸው ነው መሰለኝ ልጅ ወጣላቸው፡፡

ጌታዬ!

አሁን ድፍን ፊንፊኔን በግሬደር የሚምሱት የነርሱ ልጆች አይደሉም እንዴ? ሐብታቸውስ ቢኾን ቁጥር ስፍር አለው እንዴ? ገንዘባቸውስ ቢባል፣ እንኳንስ ኮሳሳ የባንክ ሠራተኛ ይቅርና ፈርጣማ ማሽንስ ቆጥሮ ይጨርሰዋል እንዴ?

አውቃለሁ ደላላ ብዙ ይዘላብዳል፤ እኔ እንዲያ አይደለሁም፡፡ በሬ ወለደ ወሬ አይመቸኝም፡፡ የማላውቀውን አላወራም፡፡ በካርታ አምናለሁ፡፡ በሊብሬ አምናለሁ፡፡ በካሽ አምናለሁ፡፡ በቼክ ግን አላምንም፡፡ ባልተጨበጠ ነገር አላምንም፡፡ ስለኒህ የዘሪሁን ልጆች ስነግርዎ የሚጨበጥ መረጃ ይዤ ነው!

አቢሲኒያ ዉኃ ቢሉ፣ አቢሲኒያ ቡና ቢሉ፣ አቢሲኒያ ሻይ ቢሉ፣ አ,ቢሲኒያ ቶኒክ ቢሉ፣ ኮላ ፍሬሽ ቢሉ፣ ፕሪጋት ጁስ ቢሉ፣ ኖሕ ሪልስቴት ቢሉ፣ የካቲት ወረቀት ቢሉ፣ ባለ 3፣ ባለ4 ባለ5 ኮከብ ሆቴል ቢሉ፣ ሕንጣ ቢሉ……ኸረ ይቅርብዎ ጌታዬ! እርስዎ ያልቃሉ እንጂ የነርሱ ንብረት ተቆጥሮ አያልቅም፡፡

ቦሌ ከወዳጄ ሳሚ-ጣሪያ መኖርያ ማዶ አቢሲኒያ ፕላዛ ቢሯቸው ይገኛል፡፡ 22 ከጎላጎል ወደ መገናኛ ሲሄዱ በስተቀኝ መክሊት ሕንጻ ለሆቢ የሠሩት ፎቅ ነው፡፡ ከቦሌ መድኃኒዓለም እስከ ቦሌ በሻሌ፣ ከየረር ጎሮ- አልታድ ሚካኤልን አሳብሮ፣ የነርሱ ፎቅ ያልቆመበት የፊንፊኔ ጉራንጉር አለ እንዴ?

ኸረ ጌታው! እንደው ዝም ነው የሚሻል፡፡ አንዳንድ ቤተሰብ ተባረክ ሲለው ነዳጅ በፎቅ መልክ ይቆምለታል፡፡ የጋሽ ዘሪሁን ቤተሰብ እንዲያ ነው፡፡

ትልቅዬው ጎበዝአየሁ ዘሪሁን ይባላል፡፡ ስምን መልአክ ያወጣዋል፡፡ እንዴት ያለ ጎበዝ ነጋዴ መሰለዎ!!

የካቲት ወረቀት ፋብሪካን ከፕራይቬታይዜሽን ከገዛ በኋላ እኮ በፋብሪካው ወረቀት ሳይሆን ገንዘብ ነው የሚያትመው፡፡ ሰባት ዓመት ሙሉ አርሶበታል፤ 24 ሰዓት፡፡ ደግሞ እኮ በሞተ ዋጋ ነው የገዛው፡፡ 47 ሚሊዮን ብር አሁን እንኳን ፋብሪካ 5ሺ ካሬ ባዶ መሬት ይገዛል እንዴ?

ማምኮ ሶፍትን የሚቀናቀነው ቱሊፕ የሶፍት ወረቀት የጎበዝአየሁ ምርት ነው፡፡ ፊንፊኔ የምትናፈጠው በማን ሶፍት ሆነና፡፡ ኪዮስኩን አጥለቅልቆት የለም እንዴ?

መቼ ለታ ከወፋፍራም ደላሎች ጋር መለኪያ ፉት እያልን “ጎበዝአየሁ ዘሪሁን ከቻይና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን ጋር ተጨባበጠ” የሚል ወሬ ሰምቼ በነገታው ቢሮው ድረስ ገሰገስኩኝ፡፡ “እንዴት ሳትነግረኝ፣ ጎበዜ?” ስል ወቀስኩት፡፡ ሳቀ….

“አንተኮ እንግሊዝኛ አትችልም፤ ሎካል ደላላ ነህ፡፡ ምን ብዬ ነው የምነግርህ፤ ምኑስ ይገባህና” ብሎኝ በረዥሙ ሳቀ፡፡ አልተቀየምኩትም፡፡ ሰው ላይ ይሳለቃል እንጂ ሆዱ ሸር አያውቅም፡፡

እውነት ነው፡፡ በ2 ቢሊዮን ብር አዲስ የወረቀት ፋብሪካ ሊገነባ ነው፡፡ ገላን 50ሺ ካሬ እንደተሰጠው ነገረኝ፡፡ ፋብሪካው የሚፈጀውን ብር ሲነግረኝ ግን አፌን ከፍቼ ቀረሁ፤

“ፋብሪካው ተሠርቶ ሲያልቅ አገርህ ወረቀት ከኢንዶኒዢያ ማስገባት እርግፍ አድርጋ ትተዋለች” ሲለኝ አስነጠሰኝ፡፡ ከጠረጴዛው ቱሊፕ ሶፍት አውጥቶ ሰጠኝ፡፡ ጎበዝአየሁ ጎበዝ የቢዝነስ ሰው ብቻ ሳይሆን ቀልደኛም ነው፡፡ ቀልደኛ ብቻም ሳይሆን ደግ ሰው ነው፡፡

አንድ ዕለት በአይጥማዋ ላንድክሩዘሩ ወደ ፋብሪካው እየሄድን የዚህ የአላሙዲ ነገረ-ፈጂ የአቤ ሬዲዮ የማለዳ ወሬውን ይለፍፋል፡፡ ነገሩ ሳበው መሰለኝ ሬዲዮኑን ድምጽ ጨመረለት፡፡ ታሪኩ እንኳ በርግጥም አንጀት የሚበላ ነው፡፡

ጋዜጠኛው ሕይወት ፊቷን ስላዞረችባት አንዲት እናት ነበር የሚተርከው፡፡ ይቺ እናት የወለደችው ልጅ አያድግም፡፡ አይራመድም፤ በሽተኛ ነው፡፡ ልጇን ለ16 ዓመታት አዝላው ኖራለች፣ አባት የልጁን በእግር አለመሄድ ሲመለከት አገር ጥሎ ጠፋ፣ እናት ግን እናት ናት፡፡ እንጀራ ጋግራ ለመሸጥ ስትሞክር የሰፈሩ ሰው የማያድገው ልጇን በነካችበት እጇ የጋገረችው እንጀራ አንገዛም በሚል ተጸየፈው፡፡ አልሸጥ አላት፡፡ ለ16 ዓመት ያዘለችው ልጇ የሚላስ የሚቀመስ አጣ፡፡ እሱን አዝላ ሥራ ለመሥራት መታገሏ የጎበዝአየሁን ልቡን ነካው፡፡

ወዲያውኑ መኪናውን ዳር አሲዞ ወደ ሸገር ሬዲዮ ስልክ ደውሎ ሴትዮዋን አገናኙኝ አላቸው፡፡ አድራሻዋን ሰጡት፡፡ ይቺ ሚስኪን ቀን ወጣላት፡፡ በሕይወት እስካለች ድረስ በፋብሪካው ግቢ ቋሚ ቤት ተሰጥቷት እንድትኖር፣ በደመወዝም በቋሚነት ሕይወት ዘመኗን ሙሉ በፋብሪካው መሥራት እንድትችል ትእዛዝ ሰጠላት፡፡

ገበዝአየሁ ጎበዝ የቢዝነስ ሰው ብቻ ሳይሆን ደግ ሰው ነው የምለው እንዲሁ አይደለም፡፡

ለምሳሌ ሜሪጆይ መቶ ሃያ ልጆች እንዳሉት አውቃለሁ፡፡ ሁሉ ወጪያቸውን እየቻለ የሚያሳድጋቸው እሱ ነው፡፡ የኮፊ አቢሲየኒያው ጎበዝአየሁ ደግነቱ እንደ ቡናው ፍሬ የበዛ ነው፡፡

ጋሽ ዘሪሁን ልጆቻቸው ተባርከውላቸዋል፡፡ የጎበዝአየሁ ታናናሾች ዳዊት ዘሪሁንና ቴዎድሮስ ዘሪሁንም የፊንፊኔ ነገሥታት እየሆኑ ነው፡፡ ዐይናችን እያየ አደጉ፤ ዐይናችንን ያዝ ሲያደርገው በለጸጉ፡፡ እረፍት አያውቁም፡፡ ቀንተሌት ይሠራሉ፡፡ ከሠራተኛ ጋር ጸባቸው ሰዓት ይከበር፣ ሥራ ይከበር በሚል ነው፡፡

አቢሲኒያ የማዕድን ዉኃን ገናና ያደረጉት ትንንሾቹ ዳዊትና ቴዎድሮስ ናቸው፡፡ የስዊዘርላንዱ ኔስሌ ልባቸውን አይቶ አብረን ብንሰራስ አላቸው፡፡ አሁን በሽርክና ነው ዉኃውን የሚሸጡት፡፡ ሕዝቡን የታሸገ ዉኃ እያጠጡ እነሱ ነዋይ ይጠጣሉ፡፡ ሐብታቸው ሞልቶ እየፈሰሰ ነው፡፡ ከአያት እስከ ሳርቤት፣ ከአትላስ እስከ ላምበረት፡፡ አሁን ደግሞ በ2 ሰፋፊ ካፌዎች የጀመሩት አቢሲኒያ ካፌ በመጪዎቹ ዓመታት የካልዲስ ፈተና ይሆናል ተብሏል፡፡

Noah Centrumብቻ ጌታዬ! ልጅ ከሰጠዎ እንደ ጋሽ ዘሪሁን ልጆች ይባረክልኝ ብለው ይጸልዩ!! እውነቴን ነው፡፡

ለምሳሌ ሂልተን አዲስ አበባ ሙሉ ግቢው ስንት ካሬ ነው? 60ሺ ካሉ ትክክል ነዎት፡፡ ከከዛኒቺስ ሱፐርማርኬት እስከ ግቢ ገብሬል የሚሰፋ የተንጣለለ ግቢ ነው ሂልተን ማለት፡፡ አዲሳባ እንደሂልተን ሰፊ ግቢ የትም ቦታ የላትም፡፡ የጋሽ ዘሪሁን ልጆች ግን አላቸው፡፡

ከሁለት ወር በፊት ሳር ቤት ካናዳ ኤምባሲ ጎን ያፈጣጠምኳቸው መሬት 70ሺህ ካሬ ነው የሚሰፋው፡፡ 370 ሚሊዮን ብር ሆጭ አድርገው ነው ከአንድ የጄኔራል ሚስት በካሽ የገዙት፡፡ ሳር ቤት አደባባይ ላይ እንዲህ ያለ ሰፊ ቦታ መኖሩን የሚያውቅ ሰው እንኳ ጥቂት ነው፡፡ ኸረ ከንቲባ ድሪባም ዐይተውት አያውቁም፡፡ ድሮ ሥፍራው የእርሻ ሰብል መጋዘን ነበር አሉ፡፡ አሁን በዚያ ፈረስ በሚያስጋልብ ሜዳ “ምን ሊገነቡበት ይሆን?” ብዬ ስብሰለሰል ዳዊትና ቴዎድሮስ ሚላን ከትመው፣ ከጣሊያን አርክቴክቶች ጋር እርሳስ ይዘው ቆዝመዋል አሉኝ፡፡

አዲስ አበባ በ130 ዓመት አድሜዋ ዐይታና ሰምታው የማታውቀውን ሰማይ ጠቀስ የአፓርታማ ጫካ በዚህ ስፍራ ሊገነቡበት ያስባሉ ተባልኩ፡፡

ጌታዬ! እነዚህ ልጆች የዋዛ አይምሰልዎ!

ግንባታ በጋሽ ዘሪሁን ልጆች ዘንድ የእቃ እቃ ጨዋታ ያህል አዝናኝ ነው፡፡ ሕንጻን እንደ እንጉዳይ ነው የሚያበቅሉት፡፡ በሁሉም የከተማዋ አቅጣጫ ፈጣን ግንባታ ካለ የጋሽ ዘሪሁን ሦስት ልጆች እጅ አለበት፡፡ አትላስ የገነቡት ነጩ አፓርታማ በኢትዮጵያ የመጀመርያው ነው፡፡ እነርሱ ኖሕ ሴንትረም ይሉታል፤ እኔ ግን የኖሕ መርከብ እለዋለሁ፡፡

ይሄ ሰመጠ የተባለውን ትልቁን የዓለማችን መርከብ ነው የሚመስለው፡፡ ታይታኒክን፡፡ 2500 ካሬ ላይ ያረፈ ተአምር እኮ ነው፡፡ 10ሺ ካሬ ለፓርኪንግ ለመተው ወደ ምድር አራት ቤዝመንት ቆፍረዋል፡፡ ይሄን ያህል የመኪና ማቆምያ በአሁኑ ሰዓት መስቀል አደባባይ ካልሆነ ሌላ ቦታ በፊንፊኔ የትም የለም፡፡

አትላስ ቺቺንያ አካባቢ ከእፎይ ጀርባ የሚገኝን ይሄን ገደላማ ቦታ ከአበሩስ ባለቤት-የክትፎዋ እመቤት በ18 ሚሊዮን ብር ነበር የገዟት፡፡ ተይ ይቆጭሻል ስላት አልሰማ አለች፡፡ እነርሱ ሰማይ የሚቧጥጥ መኖርያ ሠርተው በአንድ ቢሊዮን አጣሩት፡፡ ገንብተው ሲያስረክቡ ሁለት ዓመትም አልፈጀባቸው፡፡ እያንዳንዱን አፓርታማ በ5 እና በ6 ሚሊዮን ብር ነው በወረፋ የቸበቸቡት፡፡ የቤቱን ብዛት ቀበሌ ይቁጠረው፡፡

ጌታዬ! እነዚህ ሦስት ወንድማማቾች የዋዛ እንዳይመስልዎ! ምናለ ይበሉኝ ገና ጉድ ያሳዩናል፡፡

ልጆቹን ልዩ የሚያደርጋቸው ደግሞ ከሰው ብር ሳይሰበስቡ በራሳቸው አቅም ገንብተው መሸጣቸው ነው፡፡ አሁንማ ስማቸው ገኖ ገኖ ገና የግንባታ ቦታ ሲረከቡ ነው ሞጃ ሁሉ መሰለፍ የሚጀምረው፡፡ 20 ፐርሰንት ክፍል ሲባል መቶ ይሁንልኝ እያለ ለያዥ ለገናዥ የሚያስቸግሩ ደንበኞች አሉ ሲባል!!

የግንባታ ቅልጥፍናቸው የመላዕክት እርዳታ የታከለበት ነው የሚመስለው፡፡ ቦሌ መድኃኒዓለም የገነቡት አቢሲኒያ ፕላዛ  12 ፎቅ ቢረዝምም በ9ወር ነው አጽሙን ያቆሙት፡፡ የመድኃኒዓለም ጸሎተኞች ተንበርክከው ቀና ሲሉ ፎቅ አልቆ ጠበቃቸው እየተባለ ይቀለዳል፡፡

ሲኤምሲ ጀምበር ሳይት 8ሺ ካሬ ላይ ያን ሁሉ ቪላ ገንብቶ ለማስረከብ ሦስት ዓመትም አልወሰደባቸው፡፡ ይሄ ትንሹ ልጃቸው ቴዎድሮስ ይሁን ዳዊት የሚሉት ኢንጂነር ነው አሉ፡፡ እኔ እንኳ በዝና እንጂ አግኝቼውም አላውቅ፡፡ ሦስቱም ወጣቶች ናቸው፡፡ ፈዛዛ ደላላ ብዙም አይወዱም፡፡ ቢሮ አይቀመጡም፡፡ ሳይት ቆብ አጥልቀው ከቀን ሠራተኛ ጋር ሲወጡ ሲወርዱ ነው የሚውሉ፡፡

ጌታዬ! አንዳንድ ሰው አለ፤ እንኳን ሰው ጎሽ የሚታዘዝለት፡፡ ቴዎድሮስ ዘሪሁን ደግሞ አለ፣ እንኳን ሰው ቻይና ቁጭ ብድግ የሚልለት፡፡

ከመቶ በላይ እጅግ የሠለጠኑ ቻይናዊያንን አሰልፎ ደመወዝ እያበላ ወዲያ ወዲህ ያሯሩጣቸዋል፡፡ ለመጀመርያ ጊዜ ለቻይና ያዘንኩት ዳዊት ዘሪሁን ቦሌ በሻሌ አደይ አበባ የሚባለው ሳይታቸው ይዞኝ የሄደ ዕለት ነው፡፡ ላባቸው ጠብ እስቲል ነው የሚሠሩለት፡፡

እዚያ ሰፈር የሚገነቡት ቤቶች ብዛት እንደ ቻይና ሕዝብ ብዙ ነው፡፡ ቦታው 20 ሄክታር ሲሆን ከሙሌ ነው የገዙት አሉኝ፡፡ ሙለር ሪልስቴት ከቤት ግንባታው እየወጣ ከወይኑ እያበዛ ይገኛል፡፡ ከዚህ ቦብ ጊልዶፍ ከሚባል አዝማሪ ጋር ከገጠመ ወዲህ አሸሼ ገዳሜ ነው፡፡ ወይን ጠመቃው ላይ ነው የበረታ፡፡

በርግጥ ለዚህ ቦታ በምትኩ ቦሌ መድኃኒዓለም ከቢር ጋርደን ጎን፣ ከሐርመኒ ጀርባ ሆቴል ሰጥተውታል፡፡ ሊከፈት አንድ ሰንበት የቀረው፣ የስንትና ስንት የሆቴል ሠራተኛ ቅጥር የፈጸመ ባለ 4 ኮከብ ሆቴል ድንገት ሸጡለት፤ ለሙለር፡፡ ቤስት ዌስተርን ሆቴል ይባላል፡፡ ስሙ በፈረንጅ አገር እንደ ሸራተን ሂልተን እውቅ ነው አሉኝ፡፡ 4ሺ ሆቴሎችን በዓለም ያስተዳድራል ሲባል!!

ታዲያ ብልጥ አይደሉ? ከሁለቱ ሆቴሎች አንዱን ብቻ ነው ለሙሌ የሸጡለት፤ ቤስት ዌስተርን ፕላስ የሚባለውን፡፡ ከሐርመኒ ጀርባ የሚገኘውን፡፡ ከሐርመኒ ሆቴል ፊት ለፊት ያለውን ግን ለራሳቸው አስቀርተውታል፡፡ ቤስት ዌስተርን ፕሪምየም ይሰኛል፡፡ ለራስ ሲቆርሱ አያሳንሱ ነው ነገሩ፡፡

ኩቺና ፒኤልሲም የነሱ እጅ አለበት፡፡ እንደ ማክዶናልድ በዓለም የታወቀ ነው አሉ፡፡ እ-ስፐር ስቴክ ይባላል፡፡ ደቡብ አፍሪካዊ ኮርፖሬሽን ቢኾንም በዓለም በሺ የሚቆጠር ቅርንጫፍ ያለው የፋስትፉድ ቤት ነው፡፡ እነ ዳዊት በዚህ ቤት አንድ የራስ ምታት ኪኒን የምታክል በርገር በ260 ብር ይቸረችራሉ፡፡ ለዚያውም በራሳቸው ሕንጻ ላይ፡፡

የዚህ በርገር ቤት አስተናጋጆች በሙሉ ደቡብ አፍሪካ ሄደው ነው የሰለጠኑት አለኝ ጎበዝአየሁ፡፡ “ምን ልታዘዝ?” አባባልን የሚያስተምር ኮሌጅ ከዚህ ጠፍቶ ነው እዛ ድረስ የምትልኳቸው ስለው በሳቅ ተንተከተከ፡፡ ለምን እንደሁ አላውቅም ሐብታም ሲስቅልኝ ልቤ እንደ ቮልስ ሞተር ትሞቃለች፣ እንደ ቂቤ ትቀልጣለች፡፡ ኩራት ኩራት ይለኛል፡፡

ጌታዬ!!

“ደዝን፣ ገንባ፣ አስረክብ” የሚል ፍልስፍናን የሚከተሉት የጋሽ ዘሪሁን ልጆች አትላስ ከአውሮፓ ኅብረት ቢሮ ፊት ለፊት፣ ቀድሞ ዶዲ ሬስቶራንት የነበረበትን ቦታ 24 ሰዓት ቆፍረው በሦስት ወሩ ሦስተኛ ፎቅ ላይ ያደረሱት ሕንጻ አለ፡፡ ወደላይ 13 ይመዘዛል፣ ወደታች 3 ይወርዳል፡፡

ታዲያ በዚህ አፓርታማ ላይ ለመኖር እጅግ የናጠጡ ሀብታም መሆንን ይጠይቃል፡፡ አንዲት አሜሪካ የምትኖር እውቅ ትውልደ ኢትዮጵያዊት አርክቴክት ዲዛይናቸውን ወዳው ገና ሳይጨርሱት 5 አፓርታማ ገዝታቸዋለች፡፡ የሎንዶን ካፌው ኑርሁሴንም አንድ ሁለት አፓርታማዎችን ለማንኛውም ብሎ ይዟል፡፡ ኖሆች ሳንገነባ አንሸጥም ቢሉም አንዳንድ ጊዜ አስገድደው የሚገዙ ደንበኞች ያጋጥማሉ፡፡

ጌታዬ!

ከጠንካራ ቤተሰብ ወጥቶ ጠንካራ ሠራተኛ መሆን  ትልቅ ቦታ ላይ እንደሚያደርስ እነ ጎበዝአየሁ ህያው ምስክር ናቸው፡፡ እንዲህ የምለው ለበለጸጉ ሁሉ ጭራዬን ስለምቆላ አይደለም፡፡ ጋሽ ዘሪሁንና ቤተሰቡን በደንብ ስለማውቅ ነው፡፡

እነ ጋሽ ዘሪሁን ፈረንሳይ ለጋሲዮን ቡና ሲቆሉ አስታውሳለሁ፡፡ በ10ሺህ ብር ካፒታል ሲንፈራገጡ ትዝ ይለኛል፡፡ የጠቅላላ ሠራተኞቻቸው ብዛት 10 እንኳ አይሞላም ነበር እኮ፡፡ አንዲያውም አንድ ሰሞን የሚቆሉት ቡና ተበላሽቶባቸው፣ ቡና እናፈላለን ብለው ጉድ ፈልቶባቸው ይይዙት ይጨብጡት አጥተው ሲያማክሩኝ እንደትናንት ትዝ ይለኛል፡፡

ኾኖም ግን እጅ አልሰጡም፣ ወድቀው ተነሱ፡፡ ዛሬ የቢሊዮን ጌታ ሆነዋል፡፡ ሐብታቸውን ቆጥሮ መጨረስ፣ ይርጋጨፌ የቡና ጫካ ዉስጥ ገብቶ የቡና ፍሬን ለቅሞ እንደመጨረስ ከባድ ነው፡፡

ይበሉ ጌታዬ! ደህና ይሰንብቱ! እኔ ወደቴሌ ባር መብረሬ ነው፡፡

የሚቆጥሩት ሀብት ባይኖርዎ፣ ቆጥረው የማይጨርሱት ጤና ይስጥዎ!