Addis Ababa City Hall

በመሬት ወረራው ከተጠረጠሩት ውስጥ የታሰሩ አሉ

ዋዜማ ራዲዮ- ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ያገኘነው መረጃ እንዳሳየው ባለፉት ቀናት ብቻ በአዲስ አበባ ከተማ አራት ክፍለ ከተሞች በዘመቻ መልክ የመሬት ወረራ ተሰተውሏል። ንፋስ ስልክ ላፍቶ ፣ኮልፌ ቀራንዮ ፣ ቦሌ እና አቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተሞች የመሬት ወረራው የተደረገባቸው ክፍለ ከተሞች ናቸው። በኮልፌ ቀራንዮ እና በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተሞች የታየው የመሬት ወረራ እጅግ የከፋ መሆኑንም መረዳት ችለናል።


በአራቱም ክፍለ ከተሞች የመሬት ወረራን ሲፈጽሙ የነበሩት ወጣቶች ለጊዜው በውል ካልታወቁ አካባቢዎች በአይሱዙ ተጭነው የመጡ ናቸው ተብሏል። የመሬት ወረራውን ከፈጸሙ በሁዋላም ይዘዋቸው በመጡት መጋዝና መሰል የአናጢ እቃዎች እንጨት እየቆረጡ ቦታ ሸንሽነው ችካል በማኖር ሲከልሉ ታይተዋል።


የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ ታከለ ኡማ በጉዳዩ ላይ ከጸጥታ አካላት ፣ ከየክፍለ ከተማው አመራሮች፣ የመሬት ጉዳይ ከሚመለከታቸው የከተማው አመራሮችና ዋና ፈጻሚ አካላት ጋር በመሬት ወረራው ዙርያ ባደረጉት ግምገማ ድርጊቱ ፖለቲካዊ አላማ ያለው መሆኑ ተለይቷል።


መሬት ወራሪዎቹን ከአዲስ አበባ ከተማ ውጭ አደራጅቶ የሚልካቸው እንዳለና አዲስ አበባ ውስጥም ተቀብሎ የሚያስተባብራቸው ቡድን እንዳለም ፍንጭ እንዳለ የመስተዳድሩ አካላት ነግረውናል። የቡድኑ ማንነት ግን አልተገለጸልንም። ወጣቶቹም በእያንዳንዱ የመሬት ወረራ እንቅስቃሴያቸው በቡድን እንደሚንቀሳቀሱም ነው የሰማነው።


በአራቱ ክፍለ ከተሞችም በሶስት ቀናት ብቻ ለአረንጓዴ ስፍራነት የተከለሉ ቦታዎች ፣ የግለሰብ መኖርያዎች ; በሊዝ የተያዙ የግለሰብ ይዞታዎችና የእርሻ ማሳዎች በወረራ ተይዘዋል። ከጊዜው አጭርነት አንጻር ለጊዜው የተወረረው መሬት ሰፊ ነው ከማለት ውጭ ለጊዜው መጠኑን በቁጥር ማወቅ አንዳልተቻለ መስተዳድሩ አስታውቋል። እስካሁንም በቁጥጥር ስር የዋሉ ሰዎች አሉ።


የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ ታከለ ኡማም ለከተማው ጸጥታ ሀላፊዎች ያለምንም ልዩነት በዚህ ድርጊት ፈጻሚዎች ላይ ተመጣጣኝ እርምጃ ውሰዱ ሲሉ ትእዛዝ አስተላልፈዋል። እርምጃውም እስከ ቀጣዩ ሳምንት እንዲጠናቀቅ አሳስበዋል። [ዋዜማ ራዲዮ]