Ethiopian Army members- PHOTO-FILE
Ethiopian Army members- PHOTO-FILE

ዋዜማ ራዲዮ- በኢትዮ-ኤርትራ ድንበር በሚገኙ የተለያዩ አካባቢዎች ከትናንትና ጀምሮ የተኩስ ልውውጥ እየተካሄደ እንደሆነ እና ግጭቱም ወደለየለት ጦርነት የመቀየር አዝማሚያ እንዳለው ምንጮች ለዋዜማ ገለጹ፡፡ የተኩስ ልውውጡ የተቀሰቀሰው በጾረና እና ዛላምበሳ ግንባሮች ሲሆን ወደ ራማ አካባቢም እየተቃረበ እንደሆነ በአካባቢው የሚገኙ ምንጮች ይናገራሉ፡፡ ትናንት ምሽት የጀመረው የጾረናው ግጭት ዛሬም ቀጥሎ አሁንም ድረስ የተኩስ ድምጽ በአካባቢው እንደሚሰማ ምንጮች ያስረዳሉ፡፡ “ነገሩ ወደለየለት ጦርነት እያመራ ይመስላል” ይላል አንድ የአካባቢው ነዋሪ፡፡ የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት በትናንትናው ዕለት ከባድ መሳሪያዎችን ወደ ድንበር ሲያጓጉዝ መመልከቱንም ነዋሪው ይናገራል፡፡   

Updated- ዘግይቶ በደረሰንና ምንጮች እንደነገሩን መረጃ በፆረና አካባቢ እስከ ምሽቱ አንድ ስዓት የተኩስ ድምፅ መሰማቱ ቀጥሏል።

በጉዳዩ ላይ ላቀረብንለት የማረጋገጫ ጥያቄ የኢትዮጵያ መንግስት የውጪ ጉዳይ ሚንስቴር  “በጉዳዩ ላይ ዝርዝር መረጃ የለኝም- በቂና አስተማማኝ መረጃ እንደተገኘ ለህዝብ አሳውቃለሁ” የሚል ምላሽ ስጥቶናል። የኤርትራ ማስታወቂያ ሚንስትር ዛሬ ምሽት ባወጣው መግለጫ የኢትዮጵያ መንግስት በፆረና ግንባር ወረራ ፈፅሞብኛል ሲል መግለጫ ስጥቷል።

የግጭቱ መንስኤ ምን እንደሆነ እስካሁን በግልጽ የታወቀ ነገር ባይኖርም ድንበር አቅራቢያ ባሉ ከተሞች ነዋሪዎች ዘንድ ግን ከሶስት ቀን በፊት የኢትዮጵያውያን ወታደሮች መገደል ዜና ይናፈስ እንደነበር ምንጮች ይጠቁማሉ፡፡ ወታደሮቹ ተገደሉ የተባሉት ለኢትዮ-ኤርትራ ድንበር ጦርነት በምልክትነት በምትታየው ባድመ ነበር፡፡ ቁጥራቸው በውል ያልታወቀው ወጣት ኢትዮጵያውያን ወታደሮች ግድያው የተፈጸመባቸው በእግር ኳስ ጨዋታ ላይ ሆነው እንደነበር በከተሞቹ ይናፈስ የነበረው ዜና ያመለክታል፡፡

ከትናትናው ግጭት መቀስቀስ በፊት የወታደርም ሆነ የመሳሪያ እንቅስቃሴ በቅርብ ጊዜ በአካባቢው ላይ ተስተውሎ እንደማያውቅ የሚያስረዳው የዋዜማ ምንጭ ከትናንት ጀምሮ ግን በአድዋ፣ አክሱም፣ አዲግራት እና ሽሬ ከተሞች ወታደራዊ እንቅስቃሴዎች መታየት መጀመራቸውን ያስረዳል፡፡ ተከታትለው በሚጓዙ ወታደራዊ ካሚዮኖች የተጫኑ ወታደሮች እና ከባድ መሳሪያዎች እነዚህን ከተሞች አቆራርጠው ወደ ድንበር ቦታዎች ሲተሙ እንደሚታይ የአካባቢው ነዋሪ ያስረዳል፡፡

በኢትዮጵያ እና ኤርትራ መካከል ከተሰተው ደም አፋሳሽ ጦርነት በኋላ ላለፉት 17 ዓመታት በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለው ግንኙነት “ጦርነትም ሰላምም የሌለበት” ሆኖ ቆይቷል፡፡ የዛሬ ሁለት ሳምንት ገደማ ግን ለአድዋ ከተማ ነዋሪዎች ይህን የሚቀየር የሚመስል ዜና ተሰምቶ የከተማዋ መነጋገሪያ ሆኖ ሰነብቶ ነበር፡፡ ዜናው የትራንስፖርት ሚኒስትሩ ወርቅነህ ገበየሁን በከተማይቱ መገኘት ተከትሎ የናኘ ነበር፡፡ የፌደራል መንግስት ከአድዋ እስከ ድንበር ከተማይቱ ራማ የተዘረጋውን አስቸጋሪ መንገድ በአዲስ መልክ ለመገንባት ማቀዱን ከሚኒስትሩ የሰማው የከተማይቱ ነዋሪ “በቃ! አስመራ ገባን” ይል እንደነበር የዋዜማ ምንጭ ይገልጻል፡፡

ከኤርትራ ወገን ያሰባሰብነውን መረጃ ደግም በማስፈንጠሪያው ይመልከቱ  http://wazemaradio.com/?p=2304 

ይህ ዘገባ ሰኔ 5 በአዲስ አበባ አቆጣጠር  ከምሽቱ 1:00 ስዓት የተዘጋጀ ሲሆን መረጃ ባገኘን ስዓት ተጨማሪ መረጃ ይታከልበታል