Lema Megerssa, Head of Oromia region-FILE

ዋዜማ ራዲዮ- በምዕራብ ኦሮምያ ዞኖች ባለፉት ወራት በነበረው የፀጥታ ቀውስ ሀላፊነታቸውን አልተወጡም ተሳትፎም አድርገዋል ተብለው የተጠረጠሩ አንድ መቶ ያህል የክልሉ አመራሮችና የፀጥታ አካላት ላይ ምርመራ እየተካሄደ ሲሆን ስምንት መቶ የሚጠጉ ፖሊሶችም ስልጠና እንዲወስዱ እየተደረገ ነው።


ባለፉት ወራት የምዕራብ ወለጋ፣ ምስራቅ ወለጋ ፤ ሆሮ ጉዱሩ እና ቄለም አካባቢዎች በኦሮሞ ነፃነት ግንባር ታጣቂዎችና በመንግስት የፀጥታ ሀይሎች መካከል ከፍተኛ ግጭት እንደነበረ ይታወሳል። በዚህ ግጭት ደግሞ የዞኑ አመራሮችን ከመግደል እስከ ባንኮች ዘረፋ የሚደርስ ሰፊ ወንጀል መፈጸሙ በክልሉ መንግስት መግለጫ የተሰጠበት እንደነበርም አይዘነጋም፡፡በተለይ አባቶርቤ ተብሎ የሚጠረ ህቡዕ ቡድን የተለያዩ ግለሰቦችን በመግደል ድርጊት ተሰማርቶ እንደነበርም መንግስት ራሱ ይፋ አድርጓል።


አሁን አካባቢው ላይ በኦሮሞ ዲሞክራቲክ ፓርቲ (ኦዲፒ) እና በኦሮሞ ነጻነት ግንባር (ኦነግ) መካከል የተፈጸመውን እርቅ ተከትሎ አንጻራዊ ሰላም የወረደ መስሏል፡፡ ሁለቱን ወገኖች በማሸማገል ስራ ላይ የነበሩት አባ ገዳዎች እና ሃደ ሲንቄዎችም( እናቶች) ውጥረት እና ግጭት ሲንጣቸው በነበሩ ዞኖች ተንቀሳቅሰው ባሳለፍነው ሳምንት ሁኔታውን መቃኘታቸው ይታወቃል፡፡ ታጥቀው የነበሩ የኦነግ አባላትንም ትጥቅ በማስፈታት ወደተዘጋጀላቸው ካምፕ እንዲገቡ እየተደረገ ነው። ከሁሉም በላይ ግን የጠቅላይ ሚኒስትር አቢይ አህመድ እና የክልሉ ርእሰ መስተዳድር አቶ ለማ መገርሳ አካባቢው ድረስ በመጓዝ ያደረጉት ጉብኝት እና ከአካባቢው ነዋሪዎች ጋር የነበራቸው ውይይት ይበልጥ በስፍራው የሰላም አየር መንፈስ መጀመሩን ለማመላከት የታሰበ ይመስላል፡፡


አሁን ይህ ውጤት ይገኝ እንጂ ለወራት የተስተዋለውን ግጭት ያባባሰው እና ለቁጥጥር አዳጋች ያደረገው ቁጥራቸው ቀላል የማይባሉ የክልሉ የጸጥታ አካላት በሁከቱ መሳተፋቸው መሆኑን ዋዜማ ያገኘቸው መረጃ ያመለክታል፡፡ በተለይ አባቶርቤ ተብሎ ሲንቀሳቀስ በነበረው የህቡዕ ቡድን ውስጥም ሆነ አከባቢው ላይ በነበረው ሁከት የቀጥታ ተሳትፎ ነበራቸው ተብለው የተጠረጠሩ ከ800 በላይ የኦሮሚያ ክልል የፖሊስ አባላት በአሁኑ ወቅት አምቦ በሚገኘው ሰንቀሌ ወታደራዊ ማሰልጠኛ የተሃድሶ ስልጠና እየተሰጣቸው እንደሚገኝም ጭምር ነው ዋዜማ ከምንጮቿ ያረጋገጠችው፡፡


ምንጮቻችን እንደሚሉት ይበልጥ ሁከቱን በመምራት በማደራጀትና በማስተባበር አባቶርቤ በተሰኘው ቡድን ውስጥም በቀጥታ በመሳተፍ ደግሞ በ100 ግለሰቦች ላይ ምርመራ እየተካሄደባቸው ይገኛል፡፡ ከነዚህ መካከልም የዞን አመራሮች እና በፖሊስ አመራርነት ደረጃ የሚገኙ መኖራቸው ጭምርም ታውቋል፡፡ አካባቢውን ያረጋጋሉ ተብለው ከአዲስ አበባ የተላኩት የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን አመራርም ተጠርጥረው በምርመራ ላይ ናቸው፡፡ [ዋዜማ ራዲዮ]