Kifle Horo

ዋዜማ ራዲዮ- ኢንጂነር ስመኘው በቀለ የሕዳሴ ግድብ ስራ አስኪያጅነትን ሙሉ በሙሉ ጠቅለው እንዲይዙ የተደረገው የብረታብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽንን(ሜቴክ) ጥቅም አይጋፉም በሚል ተስፋ ነበር።

ኢንጂነር ስመኘው ከህልፈተ ህይወታቸው ጥቂት ቀናት አስቀድሞ ስለሚመሩት ፕሮጀክት ዝርዝር ሪፖርት አዘጋጅተው እንዲያቀርቡ ይታዘዛሉ። በተመሳሳይ ጊዜ የመንግስት የልዑካን ቡድን ወደ ሕዳሴው ግድብ መገናኛ ብዙሀንን ይዞ በመሄድ እንደሚጎበኝ መርሀ ግብር ይወጣል።

ኢንጅነር ስመኘው ለመንግስት ለማቅረብ ለተዘጋጁት ሪፖርት ከእናት መስሪያ ቤታቸው የኤሌክትሪክ ሀይል ኮርፖሬሽንና ከተቋራጩ ሜቴክ የፋይናንስ መረጃዎችን ለማስታረቅ ወደላይ ወደታች እያሉ በነበረበት ወቅት ከሜቴክ ቀና ምላሽ አላገኙም። “አለቆች የሉም” ፣ “ለማዘጋጀት ጊዜ ያስፈልገናል”  የሚሉ ምክንያቶች ተነግሯው ሲጠባበቁ የሪፖርት ማቅረቢያው ጊዜ ደረሰ።  ሌላው ተቋራጭ ሳሊኒ የራሱን ሪፖርት አስቀድሞ አስረክቦ ነበር።

ኢንጂነር ስመኘው በእጃቸው ያለውንና የሚያውቁት የፋይናንስ መረጃ ብቻ አሰናዱ። ሪፖርቱን ለማቅረብ አንድ ቀን ሲቀራቸው በጠቅላይ ሚንስትሩ ቢሮ በኩል በርካታ መረጃ  መሰባሰቡንና የህዳሴው ግድብ ስራ ከተቋረጠ ከዓመት በላይ ማስቆጠሩ መሰማቱን ደረሱበት። በሜቴክ ላይም የሙስና ምርመራ ይደረጋል ኢንጂነር ስመኘውም ከሀላፊነታቸው እንደሚነሱ ውሳኔ ላይ መደረሱን ስምተዋል።

ይልቁንም ለምርመራ የሚያስፈልጉ ቁልፍ መረጃዎችን እንዲሰጡ እንደሚጠበቁ ተነግሯቸዋል። የሜቴክ አመራሮች ኢንጂነር ስመኘው መረጃ እንዳያገኙ ከመከላከል ባለፈ መንግስት ሊያደርገው ባሰበው ምርመራ እንዳይተባበሩ ጫና ለመፍጠርም ሙከራ ሲያደርጉ ነበር።

ኢንጂነር ስመኘው በቀለ ሀምሌ 19 , 2010 አ.ም መስቀል አደባባይ መኪናቸው ውስጥ ህይወታቸው አልፎ ተገኝተው ነበር። አጣብቂኝ ውስጥ የወደቁት ስመኘው ራሳቸውን ማጥፋታቸውን ፖሊስ አደረኩት ባለው ምርመራ ገልጿል።
ሜቴክ ለዓመታት ለፈፀመው ምዝበራ ኢንጂነር ስመኘውን በቀላሉ ማግባባትና ዝም ማሰኘት ችሎ ነበር። ኢንጂነር ስመኘው በተደጋጋሚ ሜቴክ ስራውን መስራት እንደተሳነው ለመስሪያቤታቸው ሪፖርት አድርገዋል። መረጃው ከጥቂት ሀላፊዎች ውጪ እንዳይወጣ ይጠነቀቁ ነበር።

የሕዳሴው ግድብ ፕሮጀክት መጀመሪያ ላይ ሁለት ስራ አስኪያጆች ነበሩት።

የእሳቸውን ህልፈተ ህይወት ተከትሎ የግድቡ ስራ አስኪያጅነት በጊዜያዊነት የኢንጂነር ስመኘው ምክትል በነበሩት ኤፍሬም ወልደ ኪዳን ሲመራ ከቆየ በሁዋላ  በቅርቡ ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ክፍሌ ሆራን ማግኘቱ ይታወቃል።

የህዳሴው ግድብ ዋና ስራ አስኪያጅ ሆነው የተሾሙት አቶ ክፍሌ ሆሮ ሜቴክ ኤሌክትሮ ሜካኒካል ስራን መስራት የለበትም በማለታቸው ከግድቡ ሀላፊነታቸው ተባረው የነበሩ ናቸው።

አቶ ክፍሌ ሆራ ለህዳሴው ግድብ ግንባታ ሂደት አዲስ አይደሉም ይልቅስ የግድቡን ግንባታ በበላይነት ሲመሩም የነበሩም ናቸው። የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ በኢትዮጵያውያን አቆጣጠር በ2003 አ.ም ሲጀመር ኢንጂነር ስመኘው ብቻ አልነበሩም የኘሮጀክቱ ስራ አስኪያጅ : እንዲያውም የግድቡ ፕሮጀክት ሁለት ስራ አስኪያጆች ነበረት።ኢንጂነር ስመኘው የግድቡን የሲቪል ስራ በስራ አስኪያጅነት : አቶ ክፍሌ ሆሮ ደግሞ የግድቡን የኤሌክትሮ ሜካኒካል ስራዎችን በስራ አስኪያጅነት እንዲከታተሉ ተመድበዋል።

አቶ ክፍሌ በስራ አስኪያጅነት ከአንድ አመት በላይ  ሰርተዋል።ሆኖም ትንሽ ቆይቶ የህዳሴውን ግድብ የኤሌክትሮ ሜካኒካልና ሀይድሮ ሜካኒካል ስራዎችን ማን ይስራው የሚለው ጉዳይ ትልቅ አጨቃጫቂ ጉዳይ ሆኖ ብቅ ይላል። ያኔ የሲቪል ስራውን ያከናውን የጀመረው ሳሊኒ ኢምፕሪጂሎ የኤሌክትሮ ሜካኒካል ስራው እንዲሰጠው በእጅጉ ቢፈልግም በወቅቱ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ትእዛዝ የተቋቋመው የብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽንም : ሜቴክ : ስራውን ይውሰደው የሚል ሀሳብ ይቀርባል። ህዳሴው ግድብ ሲጀመር ግን ሜቴክ ገና ከተመሰረተ አንድ አመቱ ነው።

የግድቡ ኤሌክትሮ ሜካኒካል ስራዎች ስራ አስኪያጅ አቶ ክፍሌ ታድያ ለሜቴክ ኮንትራቱ መሰጠት የለበትም ሲሉ በጽኑ ተቃውመው እንደነበር ዋዜማ ያገኘችው መረጃ ያሳያል።የእሳቸውና ሌሎች ለፕሮጀክቱ የቅርብ የነበሩ የስራ ሀላፊዎችም ልምድና ብቃት ለሌለው ሜቴክ ውሉ ሊሰጠው አይገባም የሚል አቋም ይዘዋል።በአቶ ክፍሌ ሆሮ የከረረ ተቃውሞ  ያልተስማሙት አለቆቻቸው የሜቴክን ጥቅም ለማስጠበቅ ሲባል ከሀላፊነታቸው እንዲነሱ  አድርገዋቸዋል።

ኢንጂነር ስመኘውም ሁለቱንም ስራ ደርበው የህዳሴውን ግድብ ፕሮጀክት ስራ አስኪያጅነት ይዘው ህይወታቸው እስካለፈበት ጊዜ ቀጥለዋል።የሳቸው ህይወት ሲያልፍ ታዲያ አቶ ክፍሌ ሆሮ ከነበሩበት የግል ስራ ተጠርተው የግድቡን ስራ በስራ አስኪያጅነት እንዲመሩ ተደርገዋል። ሜቴክ በአዲስ አለቆቹ እየተመራ ከግድቡ ስራ እየተቀነሰ ሲመጣ አቶ ክፍሌ ሆሮ ደግሞ ወደ ግድቡ ተመልሰዋል።