IMG_0651 2ዋዜማ ራዲዮ- ኢትዮጵያ ከሶማሊያ የወሰደችው የኦብነግ መሪ በሶማሊያ የደህንነት መስሪያ ቤት ተላልፎ መሰጠቱ ህገ ወጥ መሆኑን የሀገሪቱ ፓርላማ አጣሪ ቡድን ገለፀ።
ባለፈው ነሀሴ በሶማሊያ የፀጥታ ሀይሎች ተይዞ ለኢትዮጵያ ተላልፎ የተሰጠው የኦጋዴን ብሄራዊ ነፃነት ግንባር (ኦብነግ) ከፍተኛ አመራር አብዱራኪም ሼክ ሙሴ ተላልፎ መሰጠቱ ህገወጥ ነበር ሲል በፓርላማው የተቋቋመው አጣሪ ቡድን ይፋ ባደረገው ሪፖርቱ አስታውቋል።

በተለይም የሶማሊያ የደህንነት መስሪያ ቤት ለድርጊቱ ተባባሪ መሆኑ የሀገሪቱን ክብር የሚነካ ነበር ብሏል።
የግለሰቡ ለኢትዮጵያ ተላልፎ መሰጠት የሀገሪቱን መንግስት ላይ ከፍተኛ ተቃውሞ ያሰከተለ ሲሆን መንግስት እርምጃው ከሁለት አመት በፊት በሁለቱ ሀገሮች መካከል በተደረገ የፀጥታ ስምምነት መሰረት የተከናወነ መሆኑን ሲገልፅ ቆይቷል።
አብዲራኪም የሶማሊያና የኢትዮጵያ ጥምር ዜግነት ያለው ሲሆን እሱ የሚመራው የኦጋዴን ብሄራዊ ነፃነት ግንባር በኢትዮጵያም ሆነ በሶማሊያ በአሸባሪ ድርጅትነት ተፈርጇል።
በቁጥጥር ስር የዋለው አብዱራኪም በአሁኑ ጊዜ በኢትዮጵያ ወህኒ ቤት ባልታወቀ ቦታ ታስሮ ይገኛል።