Addis Ababa, National Theater
Addis Ababa, National Theater
  • በጎንደር አንድ ወጣት ተገድሏል

ዋዜማ ራዲዮ-በአዲስ አበባ የተቃውሞ ሰልፍ እንደሚደረግ መነገሩን ተከትሎ መንግስት ስልፉን በማናቸውም መንገድ ለማምከን እየተዘጋጀ ነው። ነገ እሁድ በአዲስ አበባ በስልጣን ላይ ያለውን ስርዓት ለመቃወም የተጠራው ስልፍ በተለያየ የሀገሪቱ አካባቢ ሲካሄድ የሰነበተው ተቃውሞ አካል ነው።

በተለያዩ የከተማዋ አካባቢዎች ከፍተኛ የፀጥታ ሀይሎች የሚታዩ ሲሆን በካምፕ የሚገኙ የሰራዊት አባላትን የማሰማራት ዕቅድ መኖሩንም የፖሊስ ምንጮች ተናግረዋል።
የፌደራል ፖሊስ ኮምሽን በበኩሉ በአዲስ አበባም ይሁን በክልሎች የሚደረጉ የተቃውሞ ስልፎችን በትጋት ለሚመክቱና መስዋዕትነት ለሚከፍሉ የፖሊስ አባላት ማካካሻና የማዕረግ እንደሚያገኙ እንደተነገራቸው የሰራዊቱ አባላት ለዋዜማ ገልፀዋል።

መንግስት የፀጥታ ሀይሎች ሊያፈግፍጉ አልያም ህዝቡን ሊደግፉ ይችላሉ የሚል ስጋት እንዳለበት ጠቋሚ ነው።

የአዲስ አበባ ፖሊስ ቅዳሜ ማምሻውን በመንግስት የመገናኛ ብዙሀን ባሰራጨው መግለጫው እሁድ የታቀደውን ሰልፍ ህገወጥ መሆኑንና በሰልፉ በሚሳተፉ ላይ እርምጃ እንደሚወስድ አስጠንቅቋል።

በሀገሪቱ የቀጠለውን ህዝባዊ አመፅ የከትሎ የምዕራባውያን ሀገራት ተከታታይ የጉዞ ገደብ ማስጠንቀቂያ እያወጡ ነው። ዜጎቻቸው ተቃውሞ ባለባቸውና ሊካሄድ በታቀደባቸው አካባቢ እንደይገኙ መክረዋል።

ወራትን ባስቆጠረውና አሁን በተባባሰው አመፅ ሳቢያ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴው ላይ አደጋ ያንዣበበት ሲሆን የውጪ ኢንቨስትመንት መቀዛቀዝ ሊከተል እንደሚችል ስጋታቸውን የሚገልፁ ባለሙያዎች ብዙዎች ናቸው።
በአዲስ አበባ በሚደረገው ስልፍ ላይ ለመሳተፍ የተዘጋጁ ሁለት ወጣቶች እንደነገሩን ከሆነ ስልፉን በሀይል ለማቆምና ለመግደል ገዢው ፓርቲ ወደኋላ እንደማይል ተርድተናል ግን ደግሞ ለውጥ ፈላጊ መሆናችንን በተግባር የምንገልፅበት ጊዜ አሁን ነው።

“በገደሉን ቁጥር እንበረታለን፣ መግደል የህዝብን ጥያቄ ሊያቆመው አይችልም፣ አሁን ጊዜው የለውጥ ነው” ይላል ከዩንቨርሲቲ ከተመረቀ አራት አመት ያስቆጠረውና ስራ ፈልጎ ማግኘት ያልሆነለት ወጣት።
በጎንደር ዛሬ ቅዳሜ ዕለት ነጭ ልብስ በመልበስ በተካሄደ ተቃውሞ ሳቢያ ቢያንስ አንድ ወጣት በፀጥታ ሀይሎች መገደሉን የአካባቢው እማኞች ተናግረዋል። ዕለቱ የቀድሞው መሪ መለስ ዜናዊ አራተኛ ሙት አመት የሚዘከርበት ነበር።