ዋዜማ ራዲዮ- የኢትዮጵያ ብሄራዊ ባንክ ትላንት ማለትም መስከረም 27 ቀን 2013 አ.ም ለሁሉም ባንኮችና አነስተኛ የብድርና ቁጠባ ተቋማት በላከው ደብዳቤ ; ማንኛውም ግለሰብ በአንድ ቀን ውስጥ ከአንድ ባንክም ሆነ የገንዘብ ተቋም ማውጣት የሚችለው ጥሬ ገንዘብ በ50 ሺህ ብር እንዲወሰን አዟል።


በኢትዮጵያ ብሄራዊ ባንክ የገንዘብ ተቋማት ዘርፍ ምክትል ገዥ አቶ ሰለሞን ደስታ ተፈርሞ የወጣው ደብዳቤ FIS/03/2020 የተሰኘው መመሪያ ላይ አንድ አንቀጽ ማሻሻያ እንደተደረገበት ያነሳል። ዋዜማ ራዲዮ ያገኘችው ይሄው ደብዳቤም : የመመሪያው አንቀጽን የማሻሻሉ አላማ የብር ኖት ለውጡን ስኬታማ ለማድረግ ያለመ እንደሆነ ይገልጻል። ሆኖም ብሄራዊ ባንኩ በመመሪያው አንድ ግለሰብ ከአንድ ባንክ በወር በጥሬው ማውጣት የሚችለውን ሁለት ሚሊየን ብር ለድርጅቶች ደግሞ ሶስት ሚሊየን ብር የሚፈቅደውን አልቀነሰም።


በተሻሻለው የመመሪያው አንቀጽ 4 ንኡስ አንቀጽ 2 መሰረትም አንድ ግለሰብ በአንድ ቀን ከአንድ ባንክም ሆነ የገንዘብ ተቋም ሊያወጣ የሚችለው ትልቁ ጥሬ ገንዘብ 50 ሺህ ብር ብቻ መሆኑ ተደንግጓል።በዚሁ አንቀጽ ውስጥ ማንኛውም ህጋዊ ሰውነት ያላቸው ማለትም ተቋማትም ሆነ አክስዮን ማህበራት በአንድ ቀን ከአንድ ባንክም ሆነ የገንዘብ ተቋም በጥሬ ማውጣት የሚችሉት ትልቁ ገንዘብ 75 ሺህ ብር መሆኑን እንዲሁ መመሪያው አስቀምጧል።

የኢትዮጵያ ብሄራዊ ባንክ ከወራት በፊት ባወጣው መመሪያ መሰረት አንድ ግለሰብ በአንድ ቀን ከአንድ ባንክም ሆነ የፋይናንስ ተቋም የሚያወጣው ጥሬ ገንዘብ እስከ 200 ሺህ ብር እንዲሆን ይፈቅድ ነበር ።በተመሳሳይ ህጋዊ ሰውነት ላላቸው ተቋማት በአንድ ቀን ከአንድ ባንክም ሆነ የገንዘብ ተቋም እንዲያወጡ የሚፈቀደው ጥሬ ገንዘብ 300 ሺህ ብር ሆኖ ቆይቷል።


ይህ ተግባራዊ እንዲሆን ለተለያዩ ባንኮችና የገንዘብ ተቋማት የተላከው ደብዳቤም ሁለት ነገሮችን ጠቋሚ እንደሆነም አንድ ስማቸው እይዳይጠቀስ የፈለጉ የባንክ ከፍተኛ ሀላፊ ነግረውናል። አንዱ መመሪው ከባንክ ውጭ የሚፈጸም ግብይትን ሊቀንስ የመቻል አቅምን መፍጠሩ ነው። ይህም ወደ ባንኮች የሚገባ ገንዘብን ሊጨምረው ይችላል። በተለይ በኢትዮጵያ በቴክኖሎጂ ገንዘብን የማዘዋወር አሰራር በበቂ ሁኔታ ባለመኖሩ ጥሬ ገንዘብ የሚያስፈልጋቸውን ግብይቶች ህጋዊ ቢሆንም እጅጉን አጨናናቂ ሊደርገው እንደሚችል ስጋትን ፈጥሯል። ህገወጥነትን ለመከላከል ግን የራሱን አስተዋጽኦ ማድረጉ አይቀርም።


በሌላ በኩል በአዲሱ መመሪያ ግለሰቦች በአንድ ቀን ከአንድ ባንክ የሚያወጡትን ገንዘብ 50 ሺህ ድረስ ማውረዱ ከገንዘብ ኖት ለውጡ በሁዋላ በሚታሰበው ልክ በገበያው ላይ ከባንክና የገንዘብ ተቋማት ውጭ አለ የሚባለው ገንዘብ ወደ ባንክ እየገባ ላለመሆኑ ማሳያም ሊሆን እንደሚችል ባለሙያው ያስረዳሉ።

ከዚህ ቀደም የኢትዮጵያ ባንኮች ማህበር ከፋይናንስ ስርአቱ ውጭ 113 ቢሊየን ብር በገበያው መሰራጨቱን ገልጿል።የብር ኖት ለውጡ ያስፈለገውም ይሄን ገንዘብ ወደ ባንኮች ለማምጣት መሆኑን መንግስት ገልጾ ነበር። ባለፈው ሳምንት መጨረሻ ላይ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ባንክ ገዥ ይናገር ደሴ (ደ/ር) የብር ለውጡ ከተደረገ ጀምሮ 14 ቢሊየን ብር ወደ ባንኮች ገብቷል የሚል መግለጫ ሰጥተዋል።

እስካሁን ባለው አካሄድም ለገንዘብ ኖት ለውጡ በተቀመጠው የሶስት ወር ገደብ ውስጥ ከባንክ ውጭ ሆነ የተባለውን ከ100 ቢሊየን ብር በላይ የሆነ ገንዘብን ወደ መደበኛ የፋይናንስ ስርአት መመለስ ላይቻል ይችላል ወይንም ከባንክ ውጭ አለ የተባለው ገንዘብ መጠን ላይ አዲስ መረጃ ያስፈልግ ይሆናል ብለዋል አስተያየታቸውን ለዋዜማ ራዲዮ የሰጡት የባንክ ባለሙያ። የተወሰኑ የንግድ ባንኮች እየሰጡት ባሉት መግለጫ በብር ለውጡ ሳቢያ አዳዲስ ደንበኞችን ያግኙ እንጂ የሚጠበቀው ሀገራዊ ግብ ብዙ ይቀረዋል ባይ ናቸው። [ዋዜማ ራዲዮ]